ግንቦት 16፣ 2007 ዓ.ም. በኢትዮጵያ በተካሄደው ጠቅላላ ምርጫ፣ በዋናዋ ከተማ አዲስ አበባ የሚገኙ መራጮች ድምጻቸውን ለመስጠት ተሰልፈው። ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው በሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ፣ በ2013 ማብቂያ ላይ ድምጽ ይሰጣሉ። (ኤ.ፒ/ ሙሉጌታ አየነ)

የ2013 የኢትዮጲያ ምርጫ፤ የጋዜጠኞች የደህንነት ኪት

በመላው ሀገሪቱ ውጥረት በነገሰበት ሁኔታ፣ በመጭው ሰኔ አጋማሽ አጠቃላይ ምርጫ ለማካሄድ፣ ኢትዮጵያ ቀን ቆርጣለች። በትግራይ ውስጥ በህዳር ወር የተከሰተው ግጭት አሁንም እንደቀጠለ ነው። የሚዲያ ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት፣ በሌሎች በርካታ ክልሎችም፣ በብሔሮችና ጎሳዎች መካካል በሚፈጠር ግጭት እና በተቃውሞዎች የተነሳ፣ መጠነ-ሰፊ ነውጦች እና ዘግናኝ አደጋዎች ታይተዋል። 

የሲፒ ጥናት እንደሚያሳየው፣ ከህዳር 22፣ 2013 ጀምሮ፣ ቢያንስ ሰባት የሚሆኑ ጋዜጠኞች ዘብጥያ ወርደዋል፤ በሲፒጄ እና በሚዲያ ዘገባዎች እንደተስነደው፣ ባለስልጣናት፣ የሰላ ሂስ በሚያካሂዱ የዜና አውታሮች ላይ ጫና እያካሄዱ ነው። ባለፈው መጋቢት ወር፣ የኢትዮጲያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን፣ ሰይመን ማርክስ የተባለውን የኒው ዮርክ ታይምስ የስራ ፈቃድ ከስረዘ በኋላ ክሀገር አባሮታልየሚዲያ ዘገባዎች እንዳመለከቱት፣ የተቆጣጣሪው መስሪያ ቤት፣ አሶሼትድ ፕሬስን ጨምሮ፣ ስለ ትግራዩ ግጭት ለዘገቡ የሚድያ አውታሮችና የዜና ወኪሎች ማስጠንቀቂያዎችን ልኳል።  

በመላው ሀገሪቱ ምርጫውን የሚዘግቡ ጋዜጠኞች የተለያዩ አደጋዎች/ስጋቶች/ችግሮች ሊገጥሟችው እንደሚችሉ ልብ ሊሉ ይገባል። ስጋቶቹም የሚከተሉትን (ግን በእነዚህ ብቻ ያልተውሰኑ) ያካትታሉ፤ ግንኙነትን ሙሉ በሙሉ ማጥፋት፤ በአመጽ ተቃውሞ፣ በጎሳ ግጭት ወይንም ወታደራዊ ግጭት መሃል መጠመድ፤ አካላዊ ትንኮሳ እና ማስፈራራት፤ ነገር መጫርና ማብሽቅ፤ እና ሰዓት እላፊን ጨምሮ በመንግስት የሚጣል የእንቅስቃሴ ገደብ። 

የሲፒጄ የአደጋ ጊዜ ቡድን፣ ይህንን የምርጫ የጥንቃቄ ኪት ምርጫውን ለሚዘግቡ ጋዜጠኞች አጠናቅሯል።  ኪቱም ለአዘጋጆች፣ ለሪፖርተሮች እና ለፎቶ ጋዜጠኞች ስለ ጠቅላላው የምርጫ ኡድት እንዴት መዘጋጀት እንዳለባቸው እና አካላዊና ዲጅታል ስጋቶችን እንዴት መቀንሰ እንደሚችሉ መረጃ ይሰጣል።  

የዚህን ሴፍቲ ኪት ፒዲኤፍ ቅጂ በአማርኛ እና በእንግሊዝኛ ማውረድ ይችላሉ።

ማውጫ

  • ግንኙነቶችና ግብአቶች/ምንጮች
  • አካላዊ ደህንነት፤ ጠቀላላ የደህንነት ምክር
  • አካላዊ ደህንነት፤ ከፖለቲካዊ ስብሰባዎች እና ህዝብ ከተሰበሰበባቸው ዝግጅቶች ሪፖርት ማድረግ
  • አካላዊ ደህንነት፤ ሕዝባዊ አመፅ ባለባቸው እና ሩቅ ስፍራዎች ውስጥ መሥራት
  • አካላዊ ደህንነት፤ ከምርጫ ጋር በተያያዘ ከሚነሱ የተቃውሞ ቦታዎች ሪፖርት ማድረግ
  • አካላዊ ደህንነት፤ ከነውጠኛ ማህበረስብ መሀል ሆኖ ሪፖርት ማድረግ
  • አካላዊ ደህንነት፤ ኮቪድ-19ን ከግምት ውስጥ ማስገባት
  • የዲጂታል ደህንነት፤ አጠቅላላ ምርጥ ተሞክሮዎች
  • የዲጀታል ደህነነት፤ መሳሪያዎቸዎን ለፖለቲካዊ የድጋፍ ሰልፍ ማዘጋጀት
  • የዲጂታል ደህንነት፤ ለግንኙነት መቋረጥ መዘጋጀት
  • የዲጅታል ደህንነት፤ እራስን ከማስገር (Phishing) ስለመከላክል 
  • የዲጂታል ጥንቃቄ፤ የመስመር ላይ ጥቃት እና የተሳሳተ መረጃ ዘመጃዎች 
  • ማጠቃላያ፤የአዘጋጆች የደህንነት ማረጋገጫ ዝርዝር

ግንኙነቶችና ግብአቶች/ምንጮች

ኢትዮጵያ ውስጥ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው ጋዜጠኞች እርዳታውን በሚከተሉት የኢሜል አድራሻዎች ማግኘት ይችላሉ፤ በሲፒጄ የአደጋ ጌዜ ፕሮግራም በኢሜል አድራሻ፤ [email protected]  ወይም በሲፒጄ የአፍሪካ ፕሮግራም በኢሜል አድራሻ፤  [email protected].

የሲፒጄ የግብዓት ማዕከል፣ የቅድመ ስራ ስምሪት ዝግጅትን እና የድህረ-ሁነት እርዳታን በተመለከተ ተጨማሪ መረጃዎችና መመሪያዎች አሉት። 

አካላዊ ደህንነት፤ ጠቅላላ የደህንነት ምክር

  • ስለ አካባቢው ታሪካዊና ወቅታዊ ህዝባዊ አመጾች/ አስከፊ ግጭቶች ጥናት ያድርጉ።  ግጭቱ፣ ልክ በአማራ ክልላዊ መንግስት፣ በኦሮሞ ልዩ ዞን እንደታየው አይነት ዘግናኝ ከሆነ፣ እቦታው ሊያጋጥመዎት ከሚቸለው አደጋ አንጻር ዜናውን በመስራት ሊገኝ የሚችለውን ጠቀሜታ ያመዛዝኑት። 
  • ብሄረዎ፣ አብራዋቸው የሚሰሩት ሰዎች ብሄር ወይም የሚሰሩበት የዜና ወኪል ወገንተኝነት፣ በአካባቢው ሰዎች ወይንም ለስራ በተሰማሩበት ክልል ውስጥ ያሉ ባለስልጣናት የጥቃት ኢላማ ሊሆነ እንደሚችሉ ግምት ውስጥ ያስግቡ።
  • ወደ አካባቢ አሽከርክረው መሄድ ካለበዎት፣ በመንገደዎ በሚያገኟቸው ቦታዋች የጸጥታ ችግር ወይንም ብጥብጥ ተከስቶ እንደነበረ ያጣሩ።  ለምሳሌ፤ ኤ2 የተባለው አውራ ጎዳና የሚያልፈው በጠብ መነሻነቷ በምትታወቀው፣ አጣየ በኩል ነው። በዛ በኩል ማሽከርከር በጣም አስጊ ከመሰለዎት እና የሚቻል ከሆነ፣ የአውሮፕላን ጉዞን እንደ አንድ አማራጭ ይወሰዱ።  
  • በአውሮፕላን የሚጓዙ ጋዜጠኞች፣ ባገር ውስጥ በረራ ሳይቀር፣ ከባድ ፍተሻ ሊያጋጥማቸው እንደሚችል ማዎቅና ለዚህም መዘጋጀት ይኖርባቻዋል። ሰለሆነም፣ ሁሌም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰነዶቻቸውን እና የፈቃድ ወረቀቶቻቸውን ከእጃቸው መለየት የለባቸውም። ለምሳሌ፣ በ2011 ዓ.ም መስከረም ወር ላይ፣ የፌደራል መንግስቱ፣ ህገ ወጥ ያለውን ምርጫ ለመዘገብ የፈለገ አንድ የጋዜጠኛ ቡድን ከአዲስ አባባ ወደ መቀሌ እንዳይበር ታግዶ ነበር። 
  • ጋዜጠኞች ለሲፒጄ እንደነገሩት፣ ባለስልጣናቱ ግንኙነትን ሙሉ በሙሉ ማቋረጥን፣ ‘እንደ አንድ የማስናከያ’ መንገድ  በመጠቀም፣ ስራ ላይ ግልፅ አደጋ  በመፍጠር፣ ቦታው ላይ የዘገባ ተግዳሮት እንዲኖር ያደርጋሉ። እንዲህ አይነት ሁኔታ ሲያጋጥመዎት፣ እንዴት ግንኙነት ማድረግ እንዳለብዎትና እየተደረጉ ስላሉ ነገሮች እንዴት ማዎቅ እንዳለበዎት ያስቡበት።   
  • የኢትዮጵያ ህግ ፈቃድ ያልተሰጠባቸውን የመገናኛ መሳሪያዎችን መጠቀም እንደ ወንጀል ስለሚቆጥር፣ መሳሪያዎቹ ላይ ባለስልጣናቱ ክትትል ሊያደርጉባቸው ይችላሉ፤ በመሆኑም፣ ኢትዮጲያ የሳተላይት ስልኮች ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይግቡ ገደብ ጥላለች። ምንም እንኳን የሳተላይት ስልኮችን ወደ ሀገሪቱ ለማስገባት የሚያስችል ፈቃድ ማግኘት አስቸጋሪ ቢሆንም፣ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ፈቃድ ሲያወጡ፣ ጋዜጠኞች ስለሚጠቀሙበት መሳሪያ ከጉዟቸው በፊት የፈቃድ ወረቀት ማግኘት ግድ ይላቸዋል። 
  • በተለይ በርጥበታማ እና በተራራማ አካባቢ የሚገኙ ትናንሽና ከመንገድ ገባ የሚሉ የኢትዮጵያ መንገዶች አዳጋች እና አደገኛ ሊሆኑ ይችላሉ።  በእንደነዚህ አይነት መንጎዶች መጓዝ ካለበዎት፣ ከመሬት ከፍ ያሉ አስተማማኝ የኪራይ፤ ጎብዝ ሾፌር ይቅጠሩ።  
  • አንዳንድ የኢትዮጵያ ቦታዎች የሚገኙት ከባህር ወለል 2,500 ሜትር (8,200 ጫማ) በላይ ነው። ወደ እነዚህ ቦታዎች መሄድ ካላበዎት፣ እራሰዎን ከአየሩ ጠባይ ጋር ለማላመድ በቂ ጊዜ ይውሰዱ፤ በቂ ውኃ ይጠጡ፤ አይጣደፉ። 
  • ለአዳር ሆቴል ለመያዝ ካሰቡ፣ አንዳንድ ሆቴሎች በእጅ ቦንብ እና በፈንጅ ጥቃት ደርሶባቸው እንደነበር ልብ ይበሉ። የዚህ አይነት ጥቃት ከደረሰባቸው መካከል፣ የሚከተሉት ይገኙበታል፤ ግራንድ ሆቴል ሪዞርት (ባህር ዳር)፤ ሶቄል ሆቴል ( ነቀምቴ) እና ፍሎሪዳ ኢንተርናሽናል ሆቴል (ጎንደር)።  ስለዚህ፣ ስለሚይዙት ሆቴል የፀጥታ ሁኔታ፣ በማን ባለቤትነት እንደሚተደደር እና የጥቃት ኢላማ የመሆን ዕድሉ እስከምን ድረስ እንደሆነ ያጣሩ (ለምሳሌ፣ አማራ ክልል ውስጥ ያንድ የትግሬ ሆቴል የመጠቃቱ ዕድል ከፍተኛ ነው።) 
  • በአንድ ሁነት ወስጥ ማን ሊገኝ እንደሚችል እና ያ ሰው እንዲሚመጣ በመነገሩ ምክንያት ምን አይነት ሁከት ሊከሰት እንደሚችል ወይንም የትኞቹ የአካባቢ/ የክልል ጉዳዮች አለመረጋጋግት ሊያስነሱ እንደሚችሉ ያጣሩ።  ብጥብጥ፣ ያለ በቂ ማስጠንቀቂያ፣ በመላው ኢትዮጵያ፣ ሊከሰት፣ ሊባባስ እና ሊዛመት እንደሚችል ልብ ይበሉ። 
  • ተገቢውን የሙያ ብቃት ማረጋገጫ እና የጋዜጠኝነት ፈቃድ ማግኘተዎን ያረጋግጡ፤
    • የውጭ ሀገር ዜጋ ከሆኑ፣ ስለ መግቢያ ቪዛ የሚመለከተውን ኤምባሲ/ የቆንስላ መሥሪያ ቤት፣ የፈቃድ ወረቀተዎን እና ይዘዋቸው ሊግቡ ስለአሰቧቸው መሳሪያዎች ደግሞ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለሰልጣንን ያማክሩ። 
    • የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም ተጨማሪ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ለሀገር ውስጥ እና ለዓለም-አቀፍ ጋዜጠኞች ይሰጣል። 
    • የሚዲያ ሠራተኞች፣ ወደ አንዳንድ የሀገሪቱ ክፍሎች ለመሄድ፣ ከክልልና ከፌደራል ባለስልጣናት ተጨማሪ ሰነዶች ማግኘት ሊያስፈልጋቸው ይችላል።  
    • ለውጭ ሀገር ጋዜጠኞች፣ የሙያ ብቃት ማረጋገጫን ለማግኘት ረዘም ያለ ጌዜ ሊወስድ ይችላል–በግንቦት ወር መጀመሪያ ላይ ሲፒጄ ያነጋገራቸው ጋዜጠኞች እንደሚሉት፣ ወደ ኢትዮጵያ ለመግባት የሚያስችላቸውን ፈቃድ ለማግኘት ለሳምንታት መቆየት ነበረባቸው።
የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፣ በኢትዮጵያ ዋና ከተማ፣ አዲስ አበባ፣ ሰኔ 16 ቀን፣ 2010 ዓ.ም. ድጋፉን ሊገልጽላቸው ለወጣው ህዝብ እጆቻቸውን በማወዛወዝ ሰላምታ ሲስጡ። (ኤ.ፒ/ ቤን ኩርቲስ)

አካላዊ ደህንነት፤ ከፖለቲካዊ ስብሰባዎች እና ህዝብ ከተሰበሰበባቸው ዝግጅቶች ሪፖርት ማድረግ

የመገናኛ ብዙሃን ሠራተኞች በፖለቲካዊ ስብሰባዎች፣ ህዝብ ከተሰበሰባበቸው ዝግጅቶች ወይም ከምርጫ ጋር በተያያዙ የተቃውሞ ሰልፎች ላይ በሚሳተፉበት ወቅት በሁከትና/ ወይም አመጽ መሃል ሊገቡና የጥቃቱም ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉ ማወቅ አለባቸው። ይህ ደግሞ በተለይ በብሔሮች መካከል አለመግባባት በሚፈጠርባቸው እና  የታጠቁ ቡድኖችና ሚሊሻዎች በሚንቀሳቀሱባቸው ወረዳዎች እና ዞኖች ሊከሰት እንደሚችል ሊገነዘቡ ይገባል።

እነዚህን አደጋዎች ለመቀነስ እንዲቻል፣ የመገናኛ ብዙሃን ሰራተኞች የሚከተሉትን የደህንነት ምክሮች ማጤን አለባቸው፤

በቦታው ላይ

  • የኢትዮጵያ ዋና የዝናብ ወቅት፣ ክረምት፣ ባመዛኙ በሰኔ ወር ይጀምራል፡፡ ሥራዎትን የሚሰሩት ከቤት ውጭ ከሆነ፣ ለራስዎ፣ የዝናብ ልብስ፤ ለመሣሪያዎቸዎ ደግሞ የዝናብ መከላከያን ይያዙ፡፡
  • ከቤት ውጭ በሚከናወኑ ዝግጅቶች ላይ የሚዘግቡ ከሆነ፣ ሰዓቱን ልብ ይበሉ– ለፀሐይ ሀሩር ሊጋለጡ እንደሚችሉ ያስታውሱ፡፡ ዝግጅቶች እስከሚጀመሩ ድረስ ለተወሰነ ጊዜ ሊያስጠብቁዎት እንደሚችሉ ልብ ይበሉ፡፡ በቂ ውኃ ይጠጡ፤ የፀሐይ መከላከያ ኮፍያ ያድርጉ፤ አስፈላጊ መስሎ ከታየዎም የፀሐይ መከላከያ ቅባቶችን ይጠቀሙ።
  • በዝግጅቶች ላይ ጠብ ይነሳል ብለው ካሰቡ ራስን ለመካላክል የሚረዱ የተለያዩ  ቁሳቁሶችን (PPE) መያዝን ያስቡ፡፡ ለበለጠ መረጃ፣ የሲፒጂን ራስን ለመካላክል የሚረዱ የተለያዩ  ቁሳቁሶችን አጠቃቀም መመሪያ (እንግሊዝኛ ብቻ) ይመልከቱ፡፡
  • ህዝቡ ወይም ፖሊስ የመገናኛ ብዙሃን ሰራተኞች ላይ ጥቃት የሚሰነዝር ከመሰለ ወይም ከሰነዘረ፣ የሚዲያ መለያ ያላባቸውን ልብሶችን አይልበሱ። አስፈላጊ ከሆነም፣ ከመሳሪያዎቸዎና ከተሽከርካሪዎቸዎ ላይ የሚዲያ መለያ ሎጎዎችን ያንሱ። 
  • ጠንካራ ሶል፣ ማሰሪያ እና በተውሰነ መልኩ የቁርጭምጭሚት ድጋፍ ያላቸውን ጠንካራ ጫማዎችን ያድርጉ፡፡ ግልጽ ጫማዎችን ወይም ማሰሪያ የሌላቸውን ጫማዎች ከማድረግ ይቆጠቡ ፡፡
  • ከሥራ ባልደረባ ጋር አብሮ መሥራት ብልህነት ነው፤ የምርጫ ሂደቶች በጣም እስኪመሽ ድረስ ሊቆዩ እንደሚችሉ ግምት ውስጥ በማስግባት፣ የሚቻለዎ ከሆነ ከሌላ ዘጋቢ ወይም ፎቶግራፍ አንሺ ጋር አብረው ለመሄድ ያስቡ፤ ጨለምለም ሲል፣ የአደጋው መጠን ይጨምራል፡፡
  • ለአደጋ የማያጋልጥዎት ከሆነ የጋዜጠኝነት ማረጋገጫ ወረቀትዎትን ያሳዩ፡፡ መታዎቂያዎትን በአንገት ላይ በሚንጠለጠል የመታዎቂያ መያዣ ከማንገት ይቆጠቡ፡፡ ክዚያ ይልቅ፣ በቀበቶዎ ላይ በመቆንጣጫ ያስይዙት ወይም መታውቂያውን ማሳየት በሚያስችል ግልጽ ቦርሳ ላይ አድርገው ክንድዎ ላይ ይሰሩት።
  • የሕዝቡን ስሜት ለመረዳት ይሞክሩ፡፡ የሚቻል ከሆነም፣ ድባቡን ለማጤን ቀደም ብለው እዝግጅቱ ቦታ የደረሱ ጋዜጠኞች ዘንድ ይደውሉ፡፡ ህዝቡ ሁከት የሚፈጥር አይነት ከሆነ፣ ጠያፍ ቃላትን ለመመከት እንዲችል አዕምሮዎትን ያዘጋጁ፡፡ ለሚደርስብዎ ጥቃት ምላሽ  ከመስጠትም ሆነ ከህዝቡ ጋር ከመላተም ይቆጠቡ።
  • የሕክምና ዕርዳታ ለማግኘት ቅርብ የሆነውን ቦታ ለይተው ይወቁ።
  • ሥራው አስቸጋሪ ወይም ፈታኝ ከሆነ ስሜትዎን አምቀው አይያዙ፡፡ ስለሁኔታው ለአለቆችዎ እና ለሥራ ባልደረቦችዎ ይንገሩዋቸው፡፡ ስለ ሁሉም ፈታኝ ተሞክሮ መነጋግር እና ማውራት በጣም አስፈላጊና በዚህ መልኩ አንዱ ከሌላው መማር እንደሚችል ይገንዘቡ።

የቦታ አያያዝንና ሁኔታን ስለመገንዘብ

  • ወደ ስፍራው በከፍተኛ ፍጥነት በመብረር ህዝቡንና የፖለቲካ እጩዎችን የጥቃት ኢላማቸው ሊያደርጉ የሚችሉ ተሽከርካሪዎችና ሞተር ብስክሌቶች እንቅስቃሴ በአይነ ቁራኛ ይከታተሉ። በ 2011 ዓ.ም በዐብይ አህመድ የፖለቲካ ድጋፍ ሰልፍ ላይ የእጅ ቦንብ ተጥሎ እንደነበር ልብ ይሏል፡፡
  • ሊፈጠር የሚችለውን የመረጋገጥ አደጋ ግምት ውስጥ በማስገባት፣ በህዝባዊ ዝግጅቶች ላይ፣ የፖለቲካ ዕጩዎች እና ሕዝቡ ካሉብት አቅጣጫ አንጻር  እርሰዎ ያሉበትን ቦታ በጥሞና ያስተውሉ።  ከስልፉ ዳር በመሆን  ሊያመልጡባቸው የሚችሉበትን መንገዶች ሁሉ ያለማቋርጥ ያስተውሉ። ሕዝቡ መገፋፋትን ከጀመረ ወይም ሥርዓት-አልባ ከሆነ ደህና ጥግ ይዘው የማምለጫ መንገዶችን መከታተለዎን ይቀጥሉ።
  • ለጥቃት ዒላማ ሊሆኑ የሚችሉ የፖለቲካ እጩዎች ወደ ህዝቡ የሚቀላቀሉ ከሆነ፣ በግርግሩ መሃል እንዳይገቡ ይጠንቀቁ። ከእጩዎቹ ለአንዱ ጥያቄ መጠየቅ ካለበዎት፣ በተቻለዎት መጠን፣ ጥያቄዎን ከአስተማማኝ ርቀት ላይ ሆነው ይጠይቁ፡፡
  • ከህዝቡ መሃል አስጊ ሊሆኑ ይችላሉ ብለው የሚያስቧቸውን ግለሰቦች በንቃት ይከታተሏቸው፡፡ ሰዎች ምን አይነት ባህሪ እያሳዩ እንዳሉ፣ ከሌሎች ጋር የመረጃ ልውውጥ እያደረጉ መሆን አለመሆኑና እንዴትስ እየተለዋውጡ እንዳሉ በአስተውሎት ይከታተሉ።  ቀልብዎ የሚነግርዎትን እያዳመጡ፣ አጠራጣሪ ከሆኑ ግለሰቦች በስተጀርባ ወይም በጎን በኩል  በመሆን አስተማማኝ ርቀተዎን ጠብቀው ይቁሙ፡፡
  • አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችን ለመለየት ይችሉ ዘንድ፣ ባቅራቢያዎ የቆሙ ተሽከርካሪዎችና በአካባቢያቸውም ሆነ በውስጣቸው ያሉትን ግለሰቦች ባንክሮ ይከታተሉ፡፡
  • በተለይ ጥቃቅን ወንጀል የተለመደ በሆነባቸው አካባቢዎች፣ በሕዝቡ መሃል ወይም በቅርብ ርቀት ሆነው  ሥራዎን በሚሠሩበት ጊዜ፣ ከኪስ አውላቂዎች ይጠንቀቁ፡፡
  • ነገሮች በድንገት ወደ አስከፊ ሁኔታ ሊቀየሩ በሚችሉበት አጋጣሚ፣ የማምለጫ ስልት ይኑረዎ፡፡ በተቻለዎ መጠን፣ ይህንን ስልትዎን እቦታው ከመድረስዎ ቀደም ብለው ለመንደፍ ይሞክሩ። ከሁሉም መውጫ መንገዶች አንጻር፣ ያሉበትን ርቀት ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ደህንነቱ ከተጠበቀ ቦታ ሆነው፣ ለምሳሌ፣ የፕሬስ ማቆያ ቦታ (ቦታው ካለ ማለት ነው) ይዘግቡ፡፡
  • ከሌሎች ጋር አብረው የሚሰሩ ከሆነ ለድንገተኛ ጊዜ  ለመገናኛት የሚይገለግለዎትን ስፍራ ለይተው ይወቁ።  ወደዚህ መገናኛ ስፍራ የሚያመሩትን ሁሉንም መንገዶች ደህንነት በአንክሮ ያጢኑ።
  • የተሽከርካሪዎን ፊት ወደ ማምለጫው አቅጣጫ በማዞር ተደራሽ እና ደህንነቱ በተጠበቀ ቦታ ላይ ያቁሙ፤ ወይም ዋስትና ያለው አማራጭ የትራንስፖርት ዘዴ እንዲኖርዎት ያድርጉ፡፡
  • ህዝቡ ነውጠኛ መሆን ክጀመረ፣ ሰዎችን ከመጠየቅም ሆነ ከህዝቡ ጋር አንድ ላይ ከመቆየት ይቆጠቡ።
ሚያዚያ 24 ቀን 21013 ዓ.ም አንድ የአማራ ሚሊሺያ አባል፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በአማራ ክልል፣ ጎንደር ከተማ ላይ ፎቶ ሲነሳ።

አካላዊ ደህንነት፤ ሕዝባዊ አመፅ ባለባቸው እና ሩቅ ስፍራዎች ውስጥ መሥራት

(ኤ.ፒ/ ቤን ኩርቲስ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ በ 2010 ስልጣን ከያዙበት ጊዜ ጀምሮ በመላው ኢትዮጵያ ግጭቶች፣ ህዝባዊ አመጾች እና ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች እየተከሰቱ ሲሆን፣ ይህንን ተክትሎም የጥላቻ ንግግሮች እና የተሳሳቱ መረጃዎችም ታሪካዊ አለመተማመንን ሲያቀጣጥሉት በጎሳና ፖለቲካ ቡድኖች መካከል ያለውን ውጥረትን ሲያጦዙት ቆይተዋል። አከባቢያዊ ወይም ክልላዊ አለመረጋጋቶችን ሲያነሳሱ ከነበሩ አይነትኛ ምክንያቶች መካከልም የመሬት ይገባኛል ግጭቶች፣የግጦሽ መሬት የመብት ጥያቄዎች ፣ የተማሪዎጭ አመጾች እና የሃይማኖት ግጭቶች ይገኙበታል፡፡

ሁከቱን ምን እንደቀሰቀሰውና ምን እንደሚያራግበው መረዳት፣ ሊፈጠሩ የሚችሉ ስፍር ቁጥር የሌላቸውን አደጋዎችን ለይቶ ለማወቅና ለመቀነስ ይረዳል።  የሁከቱ መንሰኤ፣ አልፎ አልፎ ብልጭ ድርግም የሚል የክልል ድንበሮች (በቅርቡ ሶማሌ እና አፋር ውስጥ እንደታየው) መካከል ያለ ግጭት ነው? ወይስ፣ ሃይማኖትን መሰረት ያደረገ (በኦሮሚያ ውስጥ በቅርቡ እንደተስተዋለው) ጥቃት ነው?  ወይስ ደግሞ ሲብላላ የቆየ ብሄር-ተኮር (በድሬዳዋ እና በሐረር በቅርቡ እንደተከሰተው) ውጥረት ውጤት ነው? 

የመገናኛ ብዙሃን ሠራተኞች፣ የትኛውም ቦታ (ትልቅ ከተማም ይሁን ሩቅ ቦታ የሚገኝ ወረዳ) ድንገተኛ የረብሻ አመጽ ሊያስተናግድ እንደሚችል ሊገነዘቡ ይገባል፤ ይህ ደግሞ፣ አብዛኛውን ጊዜ ያለበቂ ወይንም ያለ ምንም ማስጠንቀቂያ ሊከሰት ይችላል።

አስቀድሞ ማቀድ

  • ውጥረት ወይም ግጭት በሚኖርበት ወቅት፣ የፀጥታ ኃይሎች ወይም የአካባቢው የሚሊሻ አባላት አለመረጋገት ወደሚታየበት ቦታ መሄድን ሊክላክሉ ይችላሉ፤ ይህንን ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት ወደ  ስፍራው ስለመሄድ አለመሄድ አዋጭነት ሁሌም ይጠይቁ።  
  • በአካባቢው እይተንቀሳቀሱ ስላሉ የተለያዩ የፀጥታ ኃይሎችን እና የሚሊሻ ቡድኖችን ጥናት ያካሂዱ።  ምን ዓይነት ዩኒፎርም እንደሚለብሱ፣ ለመገናኛ ብዙኃን ሊኖራቸው ስለሚችለው አመለካከት እና በቦታው ላይ ስለሚጠቀሙባቸው ታክቲኮች ለይተው ይወቁ። እነዚህ ኃይሎችም የሚከተሉትን ሊያካትቱ ይችላሉ፤
  • የኢትዮጵያ ብሄራዊ መከላከያ ኃይል (ኢብመሀ)
  • የክልል/የመንግስት ፖሊስ ኃይላት
  • የተገንጣይ ሚሊሻዎች (ለምሳሌ፣ የኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት)
  • የውጭ ወታደራዊ ኃይል (ለምሳሌ፣ ኤርትራዊያን)
  • የክልል ልዩ ኃይል (ለምሳሌ፣ የሶማሌ ክልል ልዩ ኃይል)
  • የእርስዎን መገለጫ፣ ብሔረዎን፣ ጾታዎን እና የቀድሞ ሥራዎን–አብረዎት በተባባሪነት የሚሰሩትንም ሰዎች ጭምር (ለምሳሌ ሾፌሮች ፣ ተርጓሚዎች)–ግምት ወጥ ያስገቡ።  እንደዚህ ያሉ ነግሮች በአካባቢው ሰዎች፣ በፀጥታ ኃይሎች ወይም በሚሊሺያ ቡድኖች ክትትል እና እይታ ውስጥ  የመሆን ዕድልን ይጨምራሉ ወይ?
  • በተመደቡበት ስራ ላይ እያሉ ምክር ወይም እገዛ ሊያደርጉልዎ የሚችሉ በቦታው ላይ ካሉ ከታመኑ ሰዎች ትውውቅ ለመመስረት ይሞክሩ፡፡ በተለይ አደገኛ በሆነ አካባቢ ውስጥ የሚሰሩ ከሆነ፣ ተጨማሪ ድጋፍ የማግኘትን አስፈላጊነት ወይም ከባለስልጣናት ጋር አብረው ለመስራት ያስቡ (ይህን ማድረግ ስጋት ውስጥ የማይጥለዎት ከሆነ ማለት ነው)፡፡
  • እንደ ሰሜናዊ አፋር ክልል ባሉ ሩቅ ቦታዎች ለስራ የተሰማራ አይነት  የውጭ ዜጋ ከሆኑ፣  በ 2000 ፣ በ 2005 እና በ 2010  እንደተከስቱት አይነት የጠለፋ እና የግድያ ዒላማ ሰጋቶች ጥናት ያካሂዱ፡፡
  • ግለሰቦች፣ ሩቅ እና ብጥብጥ በሚዛባቸው አካባቢዎች ብቻቸውን እንዲሰሩ ሊጠበቅባቸው አይገባም፡፡ በቦታው ላይ ሊፈጠሩ የሚችሉ የመግባባት ችግሮችን ለማስወገድ፣ ጋዜጠኞች የክልሉን ቋንቋ ከሚናገር ሰው ጋር አብረው መሥራት አለባቸው፡፡
  • ኃይለኛ ብጥብጥ የሚጠበቅ ከሆነ፣ እንደስጋቱ መጠን፣ የመከላከያ መነጽሮች፣ የደህንነት የራስ ቆቦች ፣ የአስለቃሽ ጋዝ መተንፈሻዎች እና የመከላከያ የሰውነት አልባሳትን መጠቀምን ማሰብ ተገቢ ነው። ለበለጠ መረጃ፣ የሲፒጂን ራስን ለመካላክል የሚረዱ የተለያዩ  ቁሳቁሶችን አጠቃቀም መመሪያ (እንግሊዝኛ ብቻ) ይመልከቱ፡፡
  • ለሥራ ባልደረባዎ፣ ለጓደኛዎ ወይም ለቤተሰብዎ አባል ወዴት እንደሚሄዱ እና መቼ እንደሚመለሱ ማሳወቅዎን አይርሱ፡፡ የግንኙነት መስመሮች ያለበቂ ወይንም ያለምንም ማስጠንቀቂያ ሙሉ በሙሉ ሊቋረጡ እንደሚችሉ ግምት ውስጥ በማስገባት የመግቢያ ሰአትዎ በታሰበው ሰአት መሆን ካልቻለ፣አማራጭ መግቢያ ሰአትና ሊወስዱት የሚችሉትን ርምጃ አስቀድሞ ማዘጋጀት ይመከራል።
  •  የቦታውን አቀማመጥ በማጥናት ዋና የሁከት መናሀሪያ ሊሆኑ ይችላሉ የሚሏቸውን ስፍራዎች (ለምሳሌ፣ የከተማ አደባባይ፣ የመታሰቢያ ሐውልት ወይም አንድ የተለየ ሕንፃ) ለይተው ይወቁ ፡፡
  • ወደቦታው የሚያስገቡና የሚያስዎጡ  ማለፊያ የሌላቸውን መንገዶችን ወይም ማነቆ ቦታዎችን ለይተው ይወቁ። የጉዞ መርሃ-ግብርዎን እንደሁኒታው በማስተካክል ተቀያያሪ ያድርጉት።
  • በሲፒጄ እንተደሰነደው፣ ጋዜጠኞች እና ተርጓሚዎች ያለ ክስ ሊታሰሩ እንደሚችሉ በመገንዘብ በእስር ጊዜ ሊያነጋግሩዋቸው የሚችሉ የህግ ተወካይ ይኑረዎት።
  • የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች እና ለደህንነቸው ሲባል ማንነታቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ ሲፒጄ ያነጋገራቸው እንዳስታወቁት፣ ባለፉት የቅርብ ወራት፣ በርካታ ጋዜጠኞች በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንዲቆዩ እና ወደ ፈለጉበት ቦታ እንዳይበሩ ተክልክለዋል። ይህንን አጋጣሚ ግምት ውስጥ በማስገባት አማራጭ የጉዞ መስመሮችን ያስቡ።
  • በአካባቢው የሚገኙ የሕክምና ተቋማት በሙሉ የት የት እንድሚግኙ ለይተው ይውቁ። ትግራይ ውስጥ የሚሰሩ ከሆነ፣የድንበር የለሽ ሀኪሞች ( Médecins Sans Frontières ) እንደዘገበው በግምት ወደ 70% የሚሆኑ የጤና ተቋማት ከጥቅም ውጭ እንደሆኑ ልብ ይበሉ፡፡

መጓጓዣ እና መገልገያ መሳሪያዎች

  • የተወሰኑ ሰዓቶች ላይ እንቅስቃሴን ሊከለከሉ የሚችሉ ገደቦች ወደተጣሉባቸው አካባቢዎች ጉዞዎን ሲያቅዱ፣ እቅደዎ የሚሄዱብት አካባቢው ከጣለው የእንቀስቃሴ ገድብ ጋር እንዲጣጣም ያድርጉ፤ (በካራት እና በደቡብ ህዝቦችና ብሄር ብሀረሰቦች ክልል በሚገኘው ኮንሶ ውስጥ እንደታየው) የተወሰኑ ሰዓታት የእንቀስቃሴ ገደብ ሊጣልባቸው ይችላል።  ሲፒጄ እንደሰነደው፣ ጋዜጠኛ ዳዊት ከበደ አርአያ በታህሳስ ወር 2013 መቐለ ከተማ ውስጥ በጥይት ተመቶ መገደሉን ልብ ይሏል፡፡ የግድያው ዓላማ እስክ አሁን ደረስ ግልፅ ባይሆንም፣ ጋዜጠኛው በወቅቱ ተደንግጎ የነበረውን  የሰአት እላፊ  ጥሶ እንደነበር የአከባቢው ባለሥልጣናት ተናግረዋል። 
  • የሚጓዙበትን መልካምድር በሚገባ ይወቁ። መሬቱ ጭቃማ፣ የሚያቃጥል ሀሩር፣ ድንጋያማ ወይም ደግሞ ተራራማ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለሆነም፣ ሁል ጊዜ ለቦታው የሚስማማ ተሽከርካሪ እና ብቃት ያለውን ሹፌር ይጠቀሙ።  ብልሽት ወይም ሌላ መሰናክል ሊገጥምዎት ስለሚችል በቂ መሳሪያዎች እና መለዋዎጫዎችንም ይያዙ።
  • በሕዝባዊ አመጽ ወቅት፣  የመንገዶች መቆላለፍ እና  መዘጋት ሊያጋጥዎ ስለሚችል በተቻለ መጠን አማራጭ መንገዶችን ይጠቀሙ (ለበለጠ መረጃ ከዚህ በታች ስለ ፍተሻ ኬላዎች የሚገልጸውን ክፍል ይመልከቱ)።
  • ጉዞው የሚፈጅብዎትን ጊዜና የመድረሻ ሰአትዎን አስቀድመው ያስሉ። የሚነዱበትን የጊዜ እርዝመትና የቦታ ርቀትን በሚያስሉ በመተግበሪያዎች ላይ ብዙ አይተማመኑ፡፡ ከዚያ ይልቅ፣ ከአካባቢው የሚያገኟቸውን አስተማማኝ መረጃዎችን ይጠቀሙ።
  • ረጅም የፍተሽ ስርዓት አስፈላጊ ሆኖ በሚገኝበት ወቅት፣ ስለጉዞዎ መርሀግበር ለውጥ፣ ችግር ከመፈጠሩ በፊት፣ ለአለቆቸው ወይም ለሚያምኑት ሰው አስቀድመው ያሳዉቁ።
  • አውሮፕላን ማረፊያ ወይም ወደ አውቶቡስ መናኸሪያ በሚደርሱበት ሰአት የካባቢው ነዋሪ የታመነ ሾፌር እንዲጠብቀዎ ማድረግ ይመከራል፤ በስራ ላይ እያሉ ይህ የሚያምኑት ስው ከጎነዎ እንዳይለይ ያድርጉ። 
  • በተቻለ መጠን ከቦታው ጋር አብሮ የሚሄድ ተሽከርካሪን ይጠቀሙ(ለምሳሌ፣ ውድ የሆኑ የስፖርት መኪናዎች ዝቅተኛ የኑሮ ሁኔታ ባላቸው ወይም ገጠራማ አካባቢዎች ላይ አላስፈላጊ ትኩረትን ሊስቡ እንደሚችሉ ልብ ይበሉ)። 
  • በተለይ ወደ ሩቅ ስፍራዎች በሚጓዙበት ወቅት የተሟላ የመጀመሪያ እርዳታ መስጫ/ የትራወማ ኪት ይያዙ። 
  • ሁልጊዜ የተሽከርካሪዎን ፊት ለማመለጥ ወደሚመቸው አቅጣጫ አዙረው በቂ ብርሃን ባለበትና ሰው በሚበዛበት አካባቢ ያቁሙ። ጉዞ ከመጀመርዎ በፊት የተሽከርካሪዎን ውጫዊ ገጽታ በደምብ ይፈትሹ። በጣም ፈታኝ በሆኑ መንገዶች ላይ በሚያሽከረክሩበት ጊዜም እንደዚሁ ይህንኑ ፍተሻ ደጋገመው ያድርጉ።
  • የመኪናዎን የኋላ እና የጎን መስተዋቶች በመጠቀም፣ አሁንም አሁንም የአካባቢዎን ሁኔታ ይቃኙ። ሰዎች እየተከታተሉኝ ነው ብለው ከተጠራጠሩ፣ ቀልብዎ የሚነግርዎን  በማዳመጥ በተቻለ ፍጥነት አስጊ ወዳአልሆነ ቦታ ያሽከርክሩ፡፡
  • እጅግ አስፈላጊ ካልሆነ፣ የሌሊት ጉዞን ያሰዎግዱ፤ ወደሚሄዱበት ቦታም ሳይጨልም እንዲደርሱ አድርገው ጉዞዎን ያቅዱ።
  • ይዘዋቸው የሚጓዙትንም ውድ ዕቃዎች ብዛት ይመጥኑ፡፡ ሰዎች መስታዎት ሰብረው ሊገቡ ስለሚችሉ ተሽከርካሪዎ ውስጥ ማንኛውንም መሳሪያ ትተው አይውረዱ።  በሚጭልምበት ወቅት፣ የወንጀል ስጋት ይበልጥ ሊጨምር እንደሚችል ያስታውሱ። 
  • ጥቃቅን የወንጀል እና የዝርፊያ አደጋዎችን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ዝግ ባለ የትራፊክ ሁኔታ፣ በመሳለጫ መንገዶችና በመብራት ላይ በሚያሽከረክሩበት ወቅት የተሽከርካሪዎ በሮች መቆለፋቸውንና መስኮቶችም መዘጋታቸውን ያረጋግጡ።
  • በሕዝብ አውቶቡሶች የሚጓዙ ከሆነ ለጥቃቅን ወንጀሎች ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉና ተሽርካሪዎቹም የሽፍቶች የጥቃት ዒላማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ልብ ይበሉ።

የአካባቢ ደህንነት እና ግንዛቤ

  • መስጊዶችን፣ አብያተ-ክርስቲያናትን ወይም የመንግስት ህንፃዎችን የመሰሉ ለጥቃት መነሻ ሊሆኑ የሚችሉ ቁልፍ ህንፃዎችን እና  ልዩ ምልክቶችን ለይተው ይወቁ፡፡
  • በተቻለ መጠን፣ በእነዚህ ለአደጋ በተጋለጡ ቦታዎች አይቆዩ። የሚፈልጉትን ነገር ካገኙ፣ ቦታዉን ባፋጣኝ ይልቀቁ፡፡
  • ስራዎ ላይ ሲሆኑ ከአካባቢው ሰው ጋር በመመሳሰልና አይን የሚስቡ ንብረትችንም ሆነ ሌሎች ትኩረት የሚስቡ ነገሮችን ማስወገድ ብልህነት ነው።
  • ጸጥ-ረጭ ባሉ፣ በቂ ብርሃን በሌላቸው እና ራቅ ባሉ አካባቢዎች (በተለይ የአደጋው መጠን ሊጨምር በሚችልበት በምሽት ወቅት) ስራዎትን ከማከናዎን ይቆጠቡ። 
  • በአንድ ቦታ ላይ ረዘም ላላ ጊዜ የሚሰሩ ከሆነ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎን በተቻለ መጠን ለመለዋወጥ ይሞክሩ። በዓላማ እና በልበ ሙሉነት ይንቀሳቀሱ። በእንቅስቃሴ ላይ እያሉ፣ ሃሳበዎን ሊሰርቁ የሚችሉ ነገሮችን ከማድረግ(ለምሳሌ፣ ስልክ ክማውራት) ይቆጠቡ። 
  • ወደ ውጭ ሲሄዱ ወይም ለመውጣት ሲያስቡ፣ እየተከታተሉዎ ያሉ ግለሰቦች እንዳሉ በጥሞና ያጢኑ፡፡ እንደ ምግብ ቤት ወይም ሆቴል ባሉ ህዝባዊ ስፍራዎች ከሰዎች መገናኘት ሲኖርበዎት፣ ሰዎች በቀላሉ እንዳይከታታሉዎት እመስኮት አጠገብ ያሉ ቦታዎች ከመቀመጥ ይቆጠቡ። ከህንጻው የሚወጡ ተሽከርካሪዎችን፣ ወደ ህንፃው የሚገቡና የሚወጡ አሽከርካሪዎች፣ ከህንጻው ውጭ አካባቢ ውር ውር የሚሉ ግለሰቦችን በንቃት ይከታተሉ። አስፈላጊ ከሆነም፣ ሊረዱዎ የሚችሉ ሰዎችን ይለዩ።  በእግርም ሆነ በተሽከርካሪ በመሆን ፎቶ እያነሱ  የሚከታተሉዎትን ሰዎች ባዓይነ ቁራኛ ይከታተሉ።
  • ለአዳር የሚቆዩበት ስፍራ፣ በተወስነ ደረጃ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ ቢሆን ይመከራል። ከተከራዩበት ቤት የሚያስዎጡ የማምለጫ መንገዶች ለይተው ይዎቁ። በህንፃው ፊት ለፊት ያሉ ክፍሎችን ላለመከራየት ይሞክሩ።

የፍተሻ ኬላዎች

በተለይ ህዝባዊ አመፅ እና ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች ባሉባቸው አካባቢዎች በወታደሮች፣ በፖሊስ ኃይሎች እና በአካባቢው ሚሊሻዎች የሚካሄዱ የፍተሻ ጣቢያዎችን በኢትዮጵያ አውራ ጎዳናዎች እና መንገዶች ላይ ማየት የተለመደ ክስተት ሊሆን ይችላል።

መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተሽከርካሪዎች እና ሰራተኞቻቸው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኬላዎች እና በተዘጉ መንገዶች ላይ የጥቃት ዒላማ ሆነዋል። በዚህ ረገድ፣ ትግራይ ወስጥ ኤም.ኤስ.ኤፍ ሰራተኞች ላይ፤  በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ደግሞ፣ በአየርላንድ የእርዳታ ኤጀንሲ (GoAL) ሰራተኞች ላይ የደርሰው ተጠቃሽ ነው። በተጨማሪም፣ ሲኤንኤን በቅርቡ እንደዘገበው፣ ከኢትዮጵያ ጦር ፈቃድ ያገኘ የጋዜጠኞች ቡድን ወደ ትግራይ አንዳንድ አካባቢዎች እንዳይገባ በኤርትራ ወታደሮች ተከልክሏል ፡፡

አጠቃላይ ደህንነት

  • በመንገደዎት ላይ ሊያጋጥሙዎ የሚችሉ የታወቁና ህጋዊ ኬላዎችን አስቀድመው ለየተው ይወቁ።
  • የሚያምኗቸውን የአከባቢውን ጋዜጠኞችና ሌሎች የሚያውቋቸውን ሰዎች በመጠየቅ ኦፊሴላዊ ያልሆኑ የፍተሻ  ኬላዎች የት ቦታ እንደሚገኙ ለማወቅ ይሞክሩ፡፡ የሚቻል ከሆነ፣ በዚያ መስመር እንዳያልፉ አድርገው ጉዞዎትን ያቅዱ፡፡
  • የአደጋው መጠን ሊጨምር ይችላል ተብሎ በሚታሰብበት ሰአት፣ በተለይም ከጨለመ በኋላ፣ ኦፊሴላዊ ያልሆኑ የፍተሻ ኬላዎች ችግር ሊፈጥሩ እንደሚችሉ በሚታመንባቸው መስመሮች ከማሽከርከር ይቆጠቡ፡፡

ምርጥ ተሞክሮዎች

  • ከፍተሻ ጣቢያ ሲደርሱ፣ ፍጥነትዎን ይቀንሱ፤ ዳር ለመያዝ ሲፈልጉ ምልክት ያሳዩ፤ ጨለማ ከሆነ፣ ደብዛዛ የፊት መብራቶችን ይጠቀሙ፤ በታዘዙበት ቦታ ላይ ያቁሙ።
  • ሁል ጊዜም እጆችዎ  በግልጽ እንዲታዩ ያድርጉ፤ ጨለማ ከሆነም የመኪናዎን የውስጥ መብራት ያብሩ።
  • እንዲከፍቱ እስኪጠየቁ ድረስ መስኮቶችዎን ዝግ አድርገው ይቆዩ፡፡
  • እንደ ሞባይል ስልኮች ያሉ ማናቸውንም መሣሪያዎች አይጠቀሙ፡፡
  • እንደ ላፕቶፖች እና ካሜራዎች ያሉ መሣሪያዎችን ከዕይታ ያርቁ፡፡ ከተጠየቁ በተሽከርካሪው ውስጥ እንደያዟቸው ያስረዱ፡፡
  • የጉዞ እና የተሽከርካሪ ሰነዶችን (ለምሳሌ፣ ፓስፖርት፣ የመንጃ ፈቃድ ፣ የተሽከርካሪ ኢንሹራንስ ፖሊሲ) ከእጄዎ አይለዩ፡፡
  • የፀሐይ መነፅር እና ኮፍያ የሚያደርጉ ከሆነ፣ የፍተሻ ኬላው ጋ ሲደርሱ ያውልቁ።
  • ረጋ ይበሉ፤ የሚያነጋግሩትን ሰው አይን አይኑን ይመልከቱ፤ በራስ መተማመንዎን ያሳዩ፤ ሁሌም በቀናነት ያናግሩ፤ መመሪያዎችን በትክክል ይተግብሩ፤ ሁሌም ትሁትና ጨዋ ይሁኑ።

ሊያስዎግዷቸው የሚገቡ፤

  • በከፈተኛ ፍጥነት ማሽከርከር፣ መኪናዎን ወዲያና ወዲህ ማጠማዘዝ ወይም ከዋናው መንገድ ታጥፎ  ለማሽከርከር መሞከር፤
  • መጮህ ወይም ግለሰቦች የሀየለኝነት ስሜት ማሳየት፤
  • ሰዎችን በሚያነጋግሩበት ጊዜ ጀርባዎን መስጠት፤
  • ለጠብ ሊዳርግ የሚችል አካላዊ እንቅስቃሴ ማሳየት (ለምሳሌ፣ በጣት መጠቆም ወይም እጅጌን መሰብሰብ)፡፡
በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ የገዢው ፓርቲ ደጋፊዎች፣ ግንቦት 17 ቀን፣ 2002 ዓ.ም. አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሀገር አቀፉን የምርጫ ድል ሲያከብሩ።  (ኤ.ፒ/ አኒታ ፓዎል)

አካላዊ ደህንነት፤ ከምርጫ ጋር በተያያዘ ከሚነሱ የተቃውሞ ቦታዎች ሪፖርት ማድረግ/መዘገብ

በ1997ቱ የኢትዮጵያ ምርጫ እንደታየው ሁሉ፣ ሕዝባዊ ሰልፎች በማንኛውም የምርጫ ዑደት ወቅት ሊከሰቱ እና በፍጥነት/በድንገት ወደሚዘገንን ሁኔታ ሊለወጡ ይችላሉ። እንዲህ ዓይነቱን ተቃውሞ የሚዘግቡ የመገናኛ ብዙሃን ሠራተኞች ለተለያዩ አደጋዎች ሊጋለጡ ይችላሉ። ይኽም የሚሆነው፣ በተቃውሞ ሰልፈኞች፣ በፀረ-ተቃዋሞው ሰልፈኞች እና ሰልፈኞችን ለመበተን ጥይት በመተኮስ እና አስለቃሽ ጭስ በመጠቀም በየሚታወቁ በፀጥታ ኃይሎች መካከል በሚነሳ ብጥብጥ የተነሳ ነው፡፡ እንደ ትግራይ ባሉ የግጭት ቀጠናዎች፣ ቀላል መሳሪያዎች ጥቅም ላይ አይውሉም ማለት አይቻልም ፡፡

አደጋውን ለመቀነስ ይቻል ዘንድ የሚዲያ ሰራተኞች የሚከተሉትን የደህንነት ምክሮች ማጤን ይገባቸዋል፤

ማቀድ

  • ለሪፖርትዎት የሚያስፈልጉዎትን ቁሳቁሶች ይለዩ፡፡ የማይጠቀሙባቸውን ቁሳቁሶች ይዞ ተቃውሞ ባለበት አካባቢ መዘዋወር ለጉዳት የመዳረግን እድል ይጨምራል ፡፡
  • ኃይለኛ ብጥብጥ የሚጠበቅ ከሆነ፣ እንደስጋቱ መጠን፣ የመከላከያ መነጽሮች፣ የደህንነት የራስ ቆቦች ፣ የአስለቃሽ ጋዝ መተንፈሻዎች እና የመከላከያ የሰውነት አልባሳትን መጠቀምን ማሰብ ተገቢ ነው። ለበለጠ መረጃ፣ የሲፒጂን ራስን ለመካላክል የሚረዱ የተለያዩ  ቁሳቁሶችን አጠቃቀም መመሪያ (እንግሊዝኛ ብቻ) ይመልከቱ፡፡
  • የአጎራባች አካባቢውን ካርታ በማጥናት፣ የቦታውን አቀማመጥ በተመለከት የቅድሚያ ጥናት ያካሂዱ። ማምለጥ ቢያስፈልግገዎት ከቦታው ሊያስወጡ የሚያስችሉ መንገዶችንና ለማምለጥ የማያስችሉዎትን ዝግ መንገዶች ይለዩ። ከሌሎች ጋር የሚሰሩ ከሆነም የአደጋ ጊዜ መሰብሰቢያ ቦታዎችን እንዲሁ ለይተው ይወቁ።
  • ግለሰቦች በተቃውሞ ሥፍራዎች ላይ ብቻቸውን እንዲሠሩ አይጠበቅባቸውም፡፡ ከሥራ ባልደረባዎ ጋር ለመስራት በመሞከር፣ ከተቆጣጣሪዎ፣ ከቤተሰብዎ ወይም ከጓደኞችዎ ጋር የስራ ስምሪት ሥነ ሥርዓት ያዘጋጁ፡፡ ከጨለመ በኋላ መሥራት የበለጠ አደገኛ ስለሚሆን፣ ከተቻለ መወገድ ይኖርበታል። ለተጨማሪ መረጃ፣ እባክዎ ለብቻቸው ለሚዘግቡ ጋዜጠኞች የተዘጋጀውን የሲፒጄን ምክር ይመልከቱ።

አለባበስ እና መሣሪያዎች

  • የውትድርና መልክ ያላቸውን መለዮዎችን፣ ለቀቅ ያሉ ልብሶችን፣ የፖለቲካ መፈክሮችን፣ የሚዲያ መለዮዎችን እና ያሉ ተቀጣጣይ ልብሶችን (ለምሳሌ፣ናይለን) አይልበሱ/አያድርጉ፡፡
  • ጠንካራ ሶል፣ ማሰሪያ እና በተውሰነ መልኩ የቁርጭምጭሚት ድጋፍ ያላቸውን ጠንካራ ጫማዎችን ያድርጉ።
  • ጠጉርዎ ረጂም ከሆነ ወደላይ ይጠቅልሉት ወይም በልብስ ውስጥ ሊገባ በሚችል መልኩ ይጎንጉኑት። ይህን ማድረግ፣ ግለሰቦች ከኋላ እንዳይጎትቱዎት ይከላከልለወታል። በአንገትዎ ላይ ሰንሰለቶችን፣ ክሮችን/ማተቦችን ወይም ጌጣጌጦችን ከማድረግ ይቆጠቡ፡፡
  • አጠቃቀሙን ካወቁበት፣ የህክምና ኪት ይያዙ፤ የሞባይል ስልክዎ ባትሪም  ሙሉ እንደሆነ ያረጋግጡ፡፡ ይህን ማድረግ ካልቻሉ፣ ተንቀሳቃሽ የኃይል ባንክ እና የስልክዎን ቻርጀር ይያዙ፡፡
  • በተቻለ መጠን የተወሰኑ መሳሪያዎችን ብቻ ይዘው ይሂዱ፤ ይህን ማድረግ በቅልጥፍና እንዲንቀሳቀሱና እና በፍጥነት መጓዝ ሲያዝፈልገዎትም ሽክም እንዳይበዛብዎ ይረደወታል።
  • የሚይዟቸውን ውድ ዕቃዎች መጠን ይገድቡ፡፡  መኪናዎን ስበረው ሊዎስዱበዎት ስለሚችሉ ማንኛውንም መሳሪያ አይተዉ፡፡ ጨለምለም ሲል፣ የአደጋው መጠን እየጨመረ እንደሚሄድ ልብ ይበሉ። 
ጥቅምት 13፣ 2012 ዓ.ም. አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የአንድ ቡድን አባላት፣ ጃዋር መሃመድ ከተባሉ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ቤት ፊት ለፊት መፈክር በማሰማትና በመጮህ ድጋፋቸውን ሲገልጹ:: (ኤ.ፕ/ ሙሉጌታ አየነ)

የቦታ አያያዝን እና የሁኔታዎች ግንዛቤ

  • ያሉበትን ቦታ ከግምት ውስጥ በማስገባት ስለ ሁኔታዎች በቂ ግንዛቤ ይኑረወት፡፡ የሚቻል ከሆነ፣ የበለጠ ደህንነትዎን ሊያረጋግጥልዎ የሚይስችል ከፍ ያለ ስፍራ ይምረጡ፡፡
  • ከዘረፋ፣ ከጥፋትና ከእሳት ቃጠሎ ጋር ተያይዘው የሚመጡት አደጋዎችን (ለምሳሌ፣ የሚወድቁ ፍርስራሾችን፣ የመስተዋት ስብርባሪዎችን እና እሳትን) ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ከህንፃዎች እና ከተሽከርካሪዎች በቂ ርቀተዎን በመጠበቅ  ለመስራት በሚያመቸዎ ቦታ ይሁኑ፡፡
  • ህዝብ በብዛት ከተሰበሰበበት ቦታ በቅርብ ርቀት ሆነው የሚሰሩ ከሆነ፣ ዳር ዳሩን ይያዙ። ለማምለጥ አዳጋች በሆነ መልኩ ወደ መሃል አይግቡ፡፡ ሁሉም ጋዜጠኞች፣ ነገሮች በፍጥነት ወደ አደገኛ ሁኔታ ሊቀየሩ እንደሚችሉ መገንዝብና ተቃውሞ ሰልፍ አካባቢ ከልክ በላይ መቆየት እንደሌለባቸው ልብ ማለት ይገባቸዋል፡፡
  • ከህዝቡ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ የባለስልጣናትን ስሜት እና ባህሪ ያለማቁረጥ ይከታተሉ፤ ያንብቡ። ፖሊስ ህዝቡ ዘንድ የመረበሽሥሜት ሲያይ (ወይም የዚህ ተቃራኒ ሲከስት) የበለጠ ጨካኝ ሊሆን ይችላል። የአድማ መበተኛ መለዮዎች የለበሱ ፖሊሶች በአካባቢው መታየት መጀመር ወይም የአድማ መበተኛ ጥይቶች ውርወራ ምልክቶች መታየት፣ የብጥብጥ መነሻ ጠቋሚዎች ናቸው፡፡ እንደዚህ አይነት ግልጽ ማስጠንቀቂያ ጠቋሚ ምልክቶች ሲያዩ፣ ቶሎ ብለው ደህንነቱ ወደተጠበቀ ቦታ ይሂዱ፤ ወይም ደግሞ፣ በፍጥነት አካባቢውን ለቀው ለመሄድ የሚያስችለዎትን እቅድ ያውጡ። 
  • በአጠቃላይ፣ የፎቶግራፍ ጋዜጠኞች ድርጌቶች በሚከዎኑብት አፍላ ቦታ ስለሚገኙ፣ ለአደጋ የተጋለጡ ናቸው። የፎቶ ጋዜጠኛ ከሆኑ፣ ከጀርባዎ ሆኖ ሁኔታዎን የሚከታተል ሰው ሊያዘጋጁ ይገባል። ስራዎን እየስሩ. አሁንም አሁንም (በየጥቂት ሴኮንዶች) ከጀርባዎ የሚሆነውን ይቃኙ። የካሜራዎን ማንገቻ አንገተዎ ውሰጥ በማንጠልጠል ፎቶግራፍ ከማንሳት  ይቆጠቡ። ያንን ባላማደርግ፣ በገዛ ማንገቻዎ ከመታነቅና ወደ መሬት ተጎትቶ ከመውደቅ እራስዎን ሊታደጉ ይችላሉ። ብዙውን ጊዜ፣ የፎቶ ጋዜጠኞች ስራቸውን ከርቀት ለመሥራት አልታደሉም፤ ስለሆንም፣ የሚፈልጉትን ፎቶ ቶሎ አንስተው ቦታውን በመልቀቅ፣ የሚያጠፉትን ጊዜ  መቀነስ ይኖርባቸዎል።
  • ለሕክምና ዕርዳታ የሚያገኙበትን በጣም ቅርብ ቦታ ለይተው ይውቁ፡፡

የአስለቃሽ ጋዝን መቋቋም

የአስለቃሽ ጋዝ ጥቃት ማስነጠስ፣ ማሳል፣ መትፋት፣ ማልቀስ እና መተንፈስን የሚገታ ንፍጥ እንዲፈጠር ሊያደርግ ይችላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ፣ በአስለቃሽ ጋዝ የተጠቁ ግለሰቦች፣ ሊያስታውኩ እና መተንፈስም ሊያቅታቸው ይችላል፡፡ እንደነዚህ አይነት ምልክቶች፣ የሚዲያ ሰራተኞችን፣ በአየር ወለድ የቫይረስ ጠብታዎች አማካይነት ለሚመጣ ለኮርኦቫይረስ በሽታ እስከ መጋለጥ ሊያደርሳቸው ይችላል፡፡ በኮቪድ-19 ተጋላጭ ምድብ ውስጥ በተዘረዘሩ እንደ አስም ባሉ የመተንፈሻ አካላት ችግር የሚሠቃዩ ግለሰቦች፣ ህዝባዊ ሁነቶችን ከመዘገብ ሊቆጠቡ ይገባል፡፡ የዚህ አይነት ችግር ያለባቸወ የሚዲያ ሰራተኞች፣ የአስለቃሽ ጭስን የመጠቀም አዝማሚያንም ሲያዩ፣ ተቃውሟቸውን ማሰማት አለባቸው። 

በተጨማሪም፣ በኤን. ፕ. አር (NPR) እንደተገለጸው እና መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፣ አስለቃሽ ጭስ፣ ግለሰቦችን፣ እንደ ኮሮናቫይረስ ላሉ በሽታ አምጪ ተህዋሲያን ይበልጥ ተጋላጭ  ሊያደርግ ይችላል።

የአስለቃሽ ጋዝ ተጋላጭነት ስለመቋቋም  እና የሚያስከትሉትን የአስከፊ ውጤቶችን በተመለከተ ተጨማሪ መመሪያ ለማግኘት፣ እባክዎን የሲፒ.ጄን  የሲቪል ዲዝኦርደር ምክረ-ሀሳብ ይመልከቱ ( CPJ’s civil disorder advisory) ይመልከቱ። 

አካላዊ ትንኮሳ እና ጥቃት

በሮይተርስ ፎቶግራፍ አንሺ ቲክሳ ነገሪ ላይ እንደተከሰተው የመገናኛ ብዙሃን ሰራተኞች በቦታው ላይ ሆነው በቀጥታ በሚዘግቡበት ጊዜ፣ በተቃዋሚዎችም ሆነ በፀጥታ ኃይሎች የአካል ጥቃት አደጋ ሊደርስባቸው እንደሚችል ከግምት ውስጥ ማስገባት አለባቸው። ጠብ አጫሪነት ሲገጥመዎት፣ የሚከተሉትን የደህንነት ምክሮችን ለመጠቀም ያስቡ፤

  • ወደ ተሰበሰበ ህዝብ መሃል ከመግባትዎ በፊት የተቃውሞ ሰልፈኞቹ በጋዜጠኞች ላይ ያላቸውን ስሜት ይገምግሙ። ጥቃት ሊያደርሱብዎ የሚችሉ ሰዎችን በንቃት ይከታተሉ፡፡ በህዝቡ ዘንድ የነውጠኝነት አዝማሚያ  ካስተዋሉ፣ በተቻለ ፍጥነት አስጊ ወዳልሆነ ስፍራ ያፈግፍጉ፡፡
  • ጠብ አጫሪዎችን ለይቶ ለማዎቅ የአካል እንቅሰቃሲያቸውን ያስተውሉ፤ የራስዎን አካላዊ  ቋንቋ በመጠቀም ሁኔታውን ለማረጋጋት ይሞክሩ።
  •  የጠብ አጫሪውን ሰው አይን አይኑን በማየት፣ እጆችዎን ባለማጣመር እና በተረጋጋ መንፈስ መናገረዎን ይቀጥሉ።
  • ሊያጠቃዎት ከሚያስብ ሰው አንድ እርምጃ ያህል ርቀትን ይጠብቁ። ይዘው ሊያጠቁዎ ቢሞክሩ፣ ጉልበት ሳያሳዩ ወደኋላ በማፈግፈግ እራስዎን ያስለቅቁ፡፡ እማይፈናፍን ጥግ ካስያዙዎትና አደጋ ላይ ከሆኑ፣ ይጩሁ፡፡
  • ጠቡ እየከረረ የሚመጣ ከሆነ፣ እጆችዎን ነፃ አድርገው ጭንቅላትዎን እየተከላከሉ እና ላለመውደቅ እየተጠነቀቁ በአጫጭር እርምጃዎች ይራመዱ፡፡ በቡድን የሚንቀሳቀሱ ከሆነ፣ አብረዎት ካሉት ሰዎች ጋር ሳይነጣጣሉ  እጀ ለእጅ ይያያዙ። 
  • ጠብ-አጫሪናትን መሰነድ ወሳኝ የጋዜጠኝነት ሥራ የሚሆንበት ጊዜ ቢኖርም፣ ሁኔታውን በማጤን ለደህንነተዎ ቅድሚያ ይስጡ። ጠብ-አጫሪ የሆኑ ግለሰቦችን ፎቶግራፍ ማንሳት ሁኔታውን ይበልጥ ሊያባብሰው እንደሚችል ልብ ይበሉ፡፡
  • ሰዎች  ሰብስብ ብለው ሊያጠቁዎ ከመጡ፣ የሚጠይቁዎትን ነገር ያስረክቧቸው፡፡ ማንኛዉም መሳሪያም ሆነ ገንዘብ ከህይወትዎ የበለጠ ዋጋ የለውም፡፡

አካላዊ ደህንነት፤ ከነውጠኛ ማህበረስብ መሀል ሆኖ ሪፖርት ማድረግ

በምርጫ ዑደት ወቅት፣ የመገናኛ ብዙሃን ሠራተኞች ለሚዲያ ሰዎች፣ ከሙያው ውጭ ለሆኑ ሰዋቸ ወይንም ደግሞ ለሚዲያ የጠላትነት ስሜት ባላቸው አካባቢዎች ወይም ማኅበረሰቦች መሃል ሆነው መስራት ሊጠበቅባቸው ይችላል። የዚህ አይነት ሰሜት ሊፈጠር የሚችለው፣ አንድ ማህበረሰብ የተሰማራባቸነ ህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎች (ለምሳሌ የጦር መሳሪያ ወይም የሰዎች ዝውውር) ለመደበቅ በሚፈልግበት ጊዜ ነው፡፡ ስለሆነም፣ እንደዚህ አይነት ማህበረሰቦች፣ ጋዜጠኞችን ሊያጋልጡን ይችላሉ በሚል ፍርሃት፣ እንደ ስጋት ሊመለከቷቸው ይችላሉ። አንዳንዶቹ ደግሞ፣ ሚዲያው በትክክል አይወክለንም የሚል ስሜት አላቸው፤ በአሉታዊ መልክ ነው ስለእኛ የሚዘግበው ብለው የሚያምኑ ወግኖችም አሉ። 

አደጋዎችን መቀነስ ማስቻል 

  • በኢትዮጵያ ውስጥ አንዳንድ ማህበረሰቦች (ለምሳሌ፣ የተወሰኑ የኦሞ የስምጥ ሸለቆ ክፍሎች፣ ራቅ ያሉ የአፋር እና የሶማሌ ክልል አካባቢዎች) የራሳቸው የአካባቢ ህጎች እና ሚሊሻዎች እንዳሏቸው ልብ ይበሉ።  በእንደዚህ ዓይነት ቦታዎች ላይ የሚሰሩ ከሆነ፣ በአካባቢው ሊያጋጥመዎ የሚችልን ማንኛውንም ችግር ለመከላከል፣ የአካባቢውን ህጎች፣ ልማዶች እና ደንቦችን በጥልቀት ማጥናት አለበዎት፡፡
  • ወደ እንደዚህ አይነት ማህበረሰቦች ለመዘገብ ከመሄድዎ በፊት፣ ሀሌም  ፈቃድ የግኙ፤ ያለእነእርሱ ግብዣ ወይንም ስላማንነተዎ የሚመሰክርልዎት ሰው በሌለበት ሁኔታ ለመዘገብ መሄድ ችግር ሊያመጣበዎት እንደሚችል ይገንዘቡ። ስለ ማህበረሰቡ እና ስለ አመለካከቱ  አስቀድመው በማጥናት፣ ለመገናኛ ብዙሃን ዘጋባዎች ምን ዓይነት ምላሽ ሊሰጡ እንደሚችሉ ያረጋግጡ፡፡ አስፈላጊ ከሆ፣ እራስዎን ዝቅ አድረገው ይቅረቡ፡፡
  • በ 2010 ዓ.ም፣ በምዕራብ ጎጃም ዞን በአማራ ክልል ውስጥ በተመራማሪዎች ላይ በደረሰው የግድያ ጥቃት እንደታየው፣ በህብረተሰቡ ውስጥ እየተዛመተ ያለ የሃሰት መረጃ ወደ ጠላትነትን ስሜት አምርቶ አስከፊ ጥቃት/የጅምላ ሊያስከትል እንደሚችል ልብ ይሏል፡፡
  • አብሮዎ በመሆን ስራዎን  በማስተባበር ሊያግዘው የሚችል ጎብዘ ያካባቢ ተውላጂ፣ የማህበረሰብ መሪ፣ በማህበሩ ዘንድ  የተከበረ  ሰው መቅጠር ብልህነት ነው፡፡ ድንገተኛ ሁኔታ ቢፈጠር፣ ሊረዳዎ የሚችል ተጽዕኖ መፍጠር የሚችል አካል ለይተው ይወቁ፡፡
  • በማህበረሰቡ ውስጥ የአልኮል ወይም የአደንዛዥ ዕፅ ያለቅጥ አጠቃቀም ካለ ወይም በከፍተኛ ደረጃ የተንሰራፋ ወንጀል ካለ፣ የማይጠበቁ አደጋዎች የመፈጠራቸው እድል እየጨመረ እንደሚሄድ ይገንዘቡ።
  • በተለይ አንድ ማህበረሰብ በጣም በአስጊ ሁኔታ ያለ ከሆነ፣ የሰውነት መከላከያ ጭምብሎች መልበስን ያስቡ፡፡
  • በተቻለ መጠን፣ በቡድን ሆነው ወይም ትክ አዘጋጅተው ወደ ስራ ይሰማሩ። እንደ አደጋው አስጊነት መጠን የሚተካዎት ሰው አስፈላጊ ከሆነ ምላሽ ለመስጠት እንዲችል በአቅራቢያዎ በሚገኝ ደህንነቱ በተጠበቀ ቦታ (ለምሳሌ ነዳጅ ማደያ) ውስጥ ሊቆይ ይችላል ፡፡
  • የአካባቢውን መልካ ምድራዊ አቀማመጥ ታሳቢ ያደረገ የስራ እቅድ ያውጡ፡፡ ሊከሰት የሚችለው አደጋ ከፍተኛ ነው  ብለው ካመኑ፣ የደህንነት ድጋፍ የሚያገኙበትን መንገድ ግምት ውስጥ ያስገቡ፡፡ በሥራዎ ላይ ትኩረት በሚያደርጉበት ጊዜ፣ እርስዎንና መሣሪያዎን ለመጠበቅ የቀጠሩት ያካባቢው ነዋሪ የስጋቱን ሁኔታ ሊከታተልለዎ ይችላል ፡፡
    • ተሽከርካሪዎን ወደ ማምለጫ አቅጣጫ አዙረው ያቁሙ፤ ከተቻለም፣ አሽከርካሪዎ ሁሌም በተጠንቀቅ ዝግጁ ይጠብቅዎት።
    • ከአሽከርካሪው ርቀው መሥራት ካለብዎ፣ እንዴት ወደዚያ መመለስ እንደሚችሉ ይወቁ። መንገዱን ለመለየት የሚረዱ ምልክቶችን ልብ ይበሉ፤ ለባልደረቦቸዎም ይንገሩ፡፡
    • ድንገተኛ አደጋ ቢገጥመዎ ሕክምና ለማግኘት ወዴት መሄድ እንዳለበዎት ለይተው ይወቁ። የመውጫ ስልትም ይኑርዎ።
  • አንድን ግለሰብ በቪዲዮ ከመቅረጽዎ ወይም ፎቶግራፍ ከማንሳትዎ በፊት ሁል ጊዜ ፈቃዱን ይጠይቁ፡፡ ሁልጊዜም የግለሰቦችን እምነቶቻቸውን እና ስጋቶቻቸውን ያክብሩ፡፡
  • በምሽት፣ ማለትም የአደጋው መጠን በከፍተኛ ፍጥነት ሊጨምር በሚችልበት ጊዜ ላይ ነውጠኛ ማህበረሰብ ውስጥ ከመስራት ይቆጠቡ ፡፡
  • በቦታው ካስፈላጊው ጊዜ በላይ አይቆዩ። የሚፈልጉትን የመረጃ ይዘት ካገኙ፣ በፍጥነት ይውጡ። ስምምነት የተድረሰበት ቁርጥ ያለ የመውጭያ እቅድ  አስቀድሞ ማዝጋጀት፣ በተባለው ጊዜ ለመውጣት ያግዛል። አንዱ የቡድንዎ አባል ምቾት እየተሰማው ካልሆነ፣ በውይይት ጊዜዎን አያባክኑ፤ ዝም በለው ፈጥነው ይውጡ፡፡
  • ለቦታው የሚስማማ፣ አክብሮት የተመላበት፣ የሚዲያ ኩባንያ መለያ የሌለው ልብስ ይልበሱ። አስፈላጊ ከሆነም ከመሳሪያዎቸዎና ከተሽከርካሪዎቸዎ ላይ የሚዲያ መለያ ሎጎዎችን ያንሱ። 
  • የሚይዟቸውን  ውድ ዕቃዎችና የገንዘብ ብዛት ይመጥኑ፡፡ ሌቦች እርስዎን ለማጥቃት እና መሣሪያዎቸዎን ለመቀማት አልመዋል? ከሆነ የሚፈልጉትን ሁሉ ያስረክቧቸው፡፡ ማንኛዉም መሳሪያ፣ ከህይወትዎ የሚስተካከል ዋጋ የለውም።
  • አጠቃቀሙን ካወቁበት፣ የህክምና ኪት ይዘው ይሂዱ።
  • ዘገባዎን ከማሰራጨተዎ/ ከማተመዎ በፊት ወደዚህ ቦታ ሊመለሱ እንደሚችሉ አይርሱ፡፡ የሰሩት ዘገባ ወደቦታው በሚመለሱበት ጊዜ ተቀባይነት እንደማያሳጣዎ ያረጋግጡ።

አካላዊ ደህንነት፤ ኮቪድ-19ን ከግምት ውስጥ ማስገባት

የምርጫ ዝግጅቶች እና ተዛማጅ የተቃውሞ ሰልፎች ላይ ከፍተኛ የህዝብ ብዛት መኖሩ የተለመደ ነው፤ በእንደዚህ አይነት ሁኔታ፣ አካላዊ ርቀትን መጠበቅ ደግሞ በጣም ፈታኝ ነው። የህብረተሰቡ አባላት የፊት መሸፈኛ ጭምብል ላይለብሱ ይችላሉ። የሚዲያ ሰራተኞችም ከሌሎች ጋዜጠኞች ጋር በትንሽ ስፍራ ተፋፍገው መስራት ሊኖርባቸው ይችላል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ መተፋፍግ፣ ጋዜጠኞችን ለቫይረሱ ጠብታዎች ሊያጋልጣቸው ይችላል። ከዚህም በላይ፣ ነውጠኛ  ሆኑ የማህበርሰቡ አባላት ሊሰድቧቸው፣ የአካላዊ ጥቃት ሊደርስባቸው እና  እላያቸውም ላይ ሊስሉባቸዉና ሊያነጥሱባቸው ይችላሉ፡፡

የሚጮሁ ወይም የሚዘምሩ ሰዎች የቫይረሱን ጠብታዎች ሊያዛምቱ እንደሚችሉ ልብ ይበሉ፤ ይህም፣ የመገናኛ ብዙሃን ሠራተኞች ለኮሮናቫይረስ በሽታ የመጋለጣቸውን ደረጃ ከፍ ያደርገዋል። 

  • እርሰዎ እንዳያዩአቸው የማይፈለጉ አካባቢዎችን ለመከልከል፣ ባለሥልጣናት፣ የኮቪድ-19 ገደቦች እና የሰአት እላፊ እገዳዎችን እንደ ሰበብ ሊጠቀሙባቸው እንደሚችሉ ይወቁ፡፡
  • በሚዘግቡበት ቦታ ላይ ምን አይነት የየኮቪድ-19 ገደቦች እንደተጣሉ ሁልጊዜም ጥናት ያካሂዱ፡፡ ገደቦች እንደየአካባቢው እና እንደየክልሉ ሊለያዩ ይችላሉ፤ ያለበቂ ወይም ያለምንም ማስጠንቀቂያ ሊለወጡም ይችላሉ። የኢትዮጵያ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በኮቪድ-19 ላይ በአገሪቱ ውስጥ ስላለው ሁኔታ በድረ-ገፁ እና በማኅበራዊ ሚዲያ ቻናሎቹ መረጃዎችን ያቀርባል፡፡ በተጨማሪም፣ የአፍሪካ ህብረት ተቋም የሆነው፣ የአፍሪካ የበሽታ ቁጥጥርና መከላከል ማዕከል ለኢትዮጵያም ጭምር የጉዞ ገደቦችን እና መስፈርቶችን የሚመለከት መረጃ ይሰጣል። በመንግስት ባለቤትነት የሚተዳደረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚያዋጣው መረጃም እንዲሁ ለተጓዦች፣ ለሌሎች አየር መንገዶች ተጓዦች ጭምር፣ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል፡፡
  • የኢትዮጵያን ምርጫ ለመዘገብ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚጓዙ ከሆነ፣ የቅርብ ጊዜ የኮቪድ-19 ምርመራ ማስረጃ እንዲያቀርቡ ሊጠየቁ ይችላሉ፤ እንደ ደረሱም፣ እማግለያ ቦታ እንዲቆዩ ሊጠየቁ  ይችላሉ። ሁልጊዜም፣ አስቀድመው፣ በቅርብ ሰለ ወጡ መስፈርቶች ያጣሩ፡፡
  • በማንኛውም በህዝብ የተጨናነቀ ሁነትና የተቃውሞ ሰልፍ፣ ደርጃውን የጠበቀ የፊትና ያፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል (ማለትም ኤን95 /ኤፍ. ኤፍ. ፒ2 መደበኛ ወይም የተሻለ ደርጃ ያለው) ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ የፊት መሸፈኛዎችን ስለማድረግ የሚወጡ የአተገባበር ጥብቅ መመሪያዎች እንደየአካባቢው ሊለያዩ እንደሚችሉ ልብ ይበሉ ፡፡
  • በስራዎ ላይ በሚቆዩበት ጊዜ፣ በተቻለ መጠን፣ እጅዎን በደምብና ቶሎ ቶሎ ሙልጭ አድርገው ይታጠቡ፡፡ ከታጠቡም በኋል እጆቸዎን በደንብ ያድርቁ። እጆቸዎን መታጠብ የማይችሉብት ሁኔታ ሲያጋጥመዎ፣ ባአልኮል የጅ ሳኒታይዘሮች፣ ያጽዷቸው፤ ይሁን እንጅ፣ ይህ አማራጭ፣ እጅ መታጣብን በመደበኛነት ሊተካ እንደማይችል ልብ ይበሉ።
  • ከስራ በኋላ፣ ሁሉም መሳሪያዎችዎ በደንብ መጽዳት አለባቸው ፡፡
  •  ወደ ቤተዎ  ከመግባትዎ በፊት፣ ልብሶቸዎን እና ጫማዎቸዎ በሙሉ መውለቅ አለባቸው፤ ከተቻለም፣ በሙቅ ውኃና እና በሳሙና ይታጠቡ፡፡

ስለኮቪድ-19 ወረርሽኝ አዘጋገብ ተጨማሪ ዝርዝር  መመሪያ  ለማግኘት፣ የሲፒጄን የኮቪድ-19 የደህንነት ማማከሪያ  (CPJ’s COVID-19 safety advisory) (የአማርኛው ትርጉም) ይመልከቱ።

ከዋና ከተማዋ አዲስ አበባ፣ በደቡብ ምስራቅ በምትገኝ አዳማ በተባለች ከተማ ውስጥ፣ ካሌብ አለማየሁ የተሰኘ የአንድ ኢንተርኔት ካፌ ባለቤት፣ ሚያዚያ 6፣ 2013 ዓ.ም ኮምፒውተር ሲነካካ።  (ኤ. ኤፍ. ፒ/ ሶላን ኮፊ)

የዲጂታል ደህንነት፤ ጠቅላላ ምርጥ ተሞክሮዎች

  • የመስመር ላይ አካውንቶቸዎ ስለራሰዎ፣ ስለ ቤተሰቦቸዎ ስለ ምንጮቸዎ በርካታ መረጃዎችን ይዘዋል። 15 ወይም ከዚያ በላይ የያዙ የይለፍ ቃላትን በመጠቅምና፣ የሁለት-ደረጃ ማረጋገጫን ( two-factor authentication ፣2FA) በማብራት የአካውንቶቸዎን ደህንነት ያረጋግጡ። የአካውንቶቸዎን ደህንነት ይበልጥ ለማረጋገጥ፣ አዘውትረው ምትክ ያስቀመጡ፤ ይዘቶቻቸውንም ያጥፉ። ይህን ማድረግ፣ እራስን ከመንታፊዎች ለመታደግ ይረዳል፡፡ ።ይህን በማድረግ፣ አካውንቶቸዎን ሌሎች መክፈት ቢችሉ እንኳ ሊያገኙ የሚችሉትን መጠን መቀነስ ይቻላል። የአካውንቶቸዎን ደህንነት ይበልጥ ለመጠበቅ ያሚያስችለዎን መረጃ ለማግኘት፣ የሲፒጄን የዲጂታል የደህንነት ኪት (የአማርኛውን ትርጉም) ይመልከቱ። 
  • የመሣሪያዎቸዎን ደህንነት ለመጠበቅና በውስጣቸው የያዟቸውን መረጃወች ከጥቃት መታደግ አስፈላጊ ነው። መሣሪያዎቸዎን በይለፍ ቃል ወይም በፒን ይቆልፉ። ኦፐሬቲንግ ሲስተመዎን፣ መተግብሪያዎቸዎን እና መፈለጊያዎቸዎን አዘውትረው ያዘምኑ። ይህን በማድረግ፣መሳሪያዎቸዎን ከተንኮል አዘል ዌር ይታደጉ::  መረጃዎቸዎ እና ይዘቶቸዎ እንዳይጠፉበዎ፣ ለመሳሪያዎቸዎ አዘውትረው ምትክ ያዛጋቹላቸው። ስለ መሳሪያ ደህንነት አጠባበቅ የበለጠ ለማወቅ፣ የሲፒጄን የዲጂታል የደህንነት ኪት ያንብቡ። 
  • ከሌሎች ጋር ደህንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ ለመግባባት የትኞቹን መሳሪያዎች እንደሚጠቀሙ መረዳቱ እርስዎ እና ምንጮቻችሁን ለመጠበቅ ወሳኝ ሊሆን ይችላል፡፡ በሚቻልበት አጋጣሚ ሁሉ፣ እንደ ሲግናል ወይም ዋትስአፕ ያሉ ከጫፍ-እስከ-ጫፍ የተመሰጠሩ የመልዕክት መላላኪያ መተግበሪያዎችን ይጠቀሙ፡፡ ጥሪዎችን፣ የድምፅ መልዕክቶችን፣ ሰነዶችን እና ፎቶዎችን ጨምሮ ሁሉም ይዘቶች በሚተላለፉበትም ወቅት ይሁን በሰርቨር ላይ በሚቀመጡበት ሰአት የተመሰጠሩ ናቸው። የሲፒጄ የዲጂታል ደህንነት ኪት፣ ከሌሎች ጋር ደህንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ እንዴት መግባባት እንደሚቻል ተጨማሪ መረጃ አለው ፡፡
  • በተንቀሳቃሽ ስልክም ሆነ በመደበኛ ስልክ በኩባንያዎ በኩል የሚመጣ ማንኛውም አጭር መልዕክት ወይም የስልክ ጥሪ ደህንነቱ ያልተጠበቀና ክትትልም ሊደረግበት እንደሚችል ይወቁ ፡፡
  • የሚጎበኟቸው ድር-ገጾች በእያንዳንዱ ዩ.አር.ኤል (https://cpj.org) መጀመሪያ ላይ የኤችቲቲፒስ (https) እና የቁልፍ ምልክት እንዳላቸው በማየት የተመሰጠሩ መሆናቸውን ያረጋግጡ። ይህን ማድረግ፣ በእርስዎ እና በገጹ መካከል ያለው ትራፊክ የተመሰጥረ መሆኑን ያረጋግጥልዎታል። እንዲሁም፣ የገጹን አፃፃፍ በመፈተሽ ድረ-ገጹ እውነተኛ መሆኑ አለመሆኑን ያረጋግጡ።
  • ስፓይዌር በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች እና ተቃዋሚዎች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት ለመፈፀም እንደዋለ ሲቲዝን ላብ ያደረገው ጥናት አመልክቷል፡፡ ይህንን ጥቃት በተሻለ መንገድ ለመከላከል፣ ጋዜጠኞች መሣሪያዎቻቸውን፣ መተግበሪያዎቻቸውን እና ብራውዘሮቻቸውን በየጊዜው ማዘመን አለባቸው። ስፓይዌሮችን እንዴት መከላከል እንደሚቻል ተጨማሪ ዝርዝሮችን ለማግኘት ከዚህ በታች በፊሺንግ ላይ ያለውን ክፍል ያንብቡ።

የዲጀታል ደህነነት፤ መሳሪያዎቸዎን ለፖለቲካዊ የድጋፍ ሰልፍ ማዘጋጀት

አንድን የድጋፍ ሰልፍ ከመዘገብዎ በፊት የመሳሪያዎን እና የመረጃዎን ደህንነት ለመጠበቅ እርምጃዎችን መውሰድ ሌሎች ስለ እርስዎ እና ስለ ምንጮችዎ መረጃ የማግኘት እድላቸውን ይቀንሰዋል ፡፡

ምርጥ ተሞክሮዎች

  • የሞባይል ስልክዎ ሙሉ ቻርጅ እንዳለው ያረጋግጡ፤ ተንቀሳቃሽ የኃይል ባንክም ይዘው ይሂዱ፡፡
  • መሣሪያዎችዎን ያዘጋጁ። በእጅ ስልክዎ እና በላፕቶፕዎ ላይ ያለው መረጃ ምን እንደሆነ እና በምን መልኩ እርስዎንም ሆነ ሌሎችን ለአደጋ ሊያጋልጥ እንደሚችል ይወቁ፡፡ መሣሪያዎችዎ ቢሰረቁ፣ ቢወረሱ ወይም ቢሰበሩ ሌሎች እንዲያገኟቸው ለማይፈልጓቸው መረጃዎች ምትክ ያስቀምጡ እና ያስወግዷቸው፡፡
  • መሣሪያዎቸዎን በይለፍ ቃል ወይም በፒን በመቆለፍ ደህንነታቸውን ይጠብቁ። ይህን ማድረግ ግን ባለስልጣናት መሳሪያዎቸዎን ከመክፈት ሊያግዳቸው እንደማይችል  ልብ ይበሉ።
  • በሁነቱ የማይጠቀሙባቸውን ማናቸውንም መተግበሪያዎች ከስልክዎ ዘግተው ያውጡ።
  • ከሌሎች ጋር መረጃን ለመለዋወጥ እንደ ሲግናል እና ዋትስአፕ ያሉ ከመጨረሻ-እስከ-መጨረሻ ምስጠራ ያላቸውን መተግበሪያዎች በሚቻልበት ሁኔታ ሁሉ ይጠቀሙ፡፡ የስልክ ውይይቶች እና ኤስኤምኤስ በሕግ አስከባሪዎች ሊጠለፉ እንደሚችሉ ይወቁ፡፡
  • በመልዕክት መላኪያ መተግበሪያዎችዎ ውስጥ ምን ይዘት እንዳለ ይውቁና ይዘቱን በመደበኛነት ምትክ ለማዘጋጀትና ለመሰረዝ የሚያስችለዎትን ሂደት ያዘጋጁ ፡፡
  • በስልክዎ እና በመልዕክት መላላኪያ መተግበሪያዎችዎ ውስጥ ያሉትን ዕውቂያዎች ይቆጣጠሩ፡፡ እርስዎን ወይም እነሱን አደጋ ላይ ሊጥሉ ይችላሉ የሚሏቸውን ሰዎች ዝርዝር መረጃዎች ያስወግዱ፡፡ እውቂያዎች በመተግበሪያዎች እና ክላውድ ውስጥ እንዲሁም በሲም ካርዱ ላይ ተከማችተው እንደሚቆዩ ልብ ይበሉ።
  • መሳሪያዎችዎን ከርቀት ለማጽዳት እንደሚችሉ አድርገው ያዘጋጁ፡፡ ምንአልባት ብያዝ ወይም ብታሰር እና በርቀት መሳሪያዎቼን ለማጽዳት ጊዜ አይኖርኝም የሚል ስጋት ካለዎት፣ በእንዲህ አይነት ሁኔታ ሃላፊነት ወስዶ ከርቀት ያጸዳልኛል ብለው ከሚያምኑት ሰው ጋር አስቅድመው መነጋገር ይኖርብዎታል፡፡ አንድ መሣሪያን ከርቀት ማጽዳት የሚቻለው ከበይነመረብ ጋር ወይም ከተንቀሳቃሽ ስልክ ዳታ ጋር ከተገናኘ ብቻ ነው። መሣሪያዎን ማጽዳት የበለጠ ተጠርጣሪ ሊያደርግዎት እንደሚችልም ልብ ይበሉ።
  • ከእይታዎ ርቀው ቆይተው ከቀናት በኋላ ሊመለሱለዎት የሚችሉ መሳሪያዎችዎ፣ በስፓይዌር ተበክለው ሊሆን ይችላል። እንደዚህ ባለ ጊዜ፣ ከተቻለ አዳዲስ መሣሪያዎችን ይግዙ። ይኽ የማይቻል ከሆነ ደግሞ፣ የስልከዎን የፋብሪካ ዳግም ማስጀመር ስራ (factory reset) ያከናውኑ፤ ይኽን ማድረግ ግን ስፓይዌሩን ሊያስወግደው እንደማይችል ልብ ይበሉ።
  • ሂደቱን ለመዘገብ የግል ስልክዎን መውሰድ የሚያሰጋዎ ከሆነ በምትኩ ረከስ ያለ ስልክ ገዝተው እሱኑ ይዘው ለመሄድ ያስቡ።
  • መሣሪያዎችዎን ያመስጥሩ፡፡ ለተጨማሪ መረጃ፣ የማመስጠርያ መሳሪያዎቸን በተመለከት፣ የሲፒጄን  መመሪያ (CPJ’s guide on encrypting devices) ይመልከቱ።
  • አካውንቶቸዎን በሁለት-ደረጃ ማረጋገጫ እና 15 ወይም ከዚያ በላይ ፊደላትን የያዙ  ረጅምና ለይት ያሉ የይለፍ ቃላት በመጠቀም ደህንነታቸውን ይጠብቁ። ከባዮሜትሪክስ ይልቅ የይለፍ ኮድዎን በመሳሪያዎችዎ ላይ ያድርጉ፡፡ የአካውንቶችን ደህንነት ማስጠበቅን በተመለከተ የሲፒጄን መመሪያ (CPJ’s guide on securing accounts) ይመልከቱ።
  • ለቀረጹት/ለሰነዱት ሁነት አዘውተረው ምትክ ያስቀምጡ፡፡ ይህን ማድረግ፣ መሣሪያዎችው ቢቀሙ ወይም ቢሰበሩ እንኳ መረጃዎን እንዳያጡ ያግዘዎታል።
  • ሁነቱ እየተካሄደ እያለ ሁነቱን ትዊት ማደርግ ወይም በቀጥታ አየር ላይ ማሰራጩት ለከፍተኛ አካላዊ አደጋ ላይ ሊጥለዎት እንደሚችል ይወቁ፡፡
  • መሣሪያዎን ሊወስዱ፣ ሊሰብሩ ወይም ሊሰርቁ ከሚፈልጉ ሰዎች ይጠንቀቁ፡፡

የዲጂታል ደህንነት፤ ለግንኙነት መቋረጥ መዘጋጀት

በሲፒጄ እንደተሰነደው፣ ኢትዮጵያ ውስጥ፣ በተለይም የፖለቲካ አለመረጋጋት በሚከሰትበት ወቅት፣ የኢንተርኔት የግንኙነት መቋረጦች የተለመዱ ናቸው። በሰኔ 2012፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ፣ ኢንተርኔት ተዘግቶ ነበር፤ እንዲህ አይነት የግንኙነት መቋረጦች በየክልሉም የተለመዱ ናቸው። በህዳር 2012 ከተፈጠረው የትጥቅ ግጭት አንስቶ፣ የትግራይ ክልል የኢንተርኔት መቋረጥ አጋጥሟታል ሲል ሲፒጄ ሰንዷል፡፡ የግንኙነት መቋረጥ ከጥቂት ሰዓታት እስከ ወራቶች ሊቆይ የሚችል ሲሆን፣ ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል መጥፋትን ሊያካትት ይችላል፤ በግንኙነቶኝ መቋረጥ ወቅት መሥራት ውስብስብ ሊሆን ቢችልም፣ ጋዜጠኞች እራሳቸውን ለዚህ ሁኔታ በማዘጋጀት፣ ሊወስዷቸው የሚችሏቸው እርምጃዎች አሉ

አጠቃላይ የዲጂታል ደህንነት ምክር

  • የመሳሪያዎችዎን ደህንነት ይጠብቁ፤ በውስጣቸው የሚያስቀምጡትንም መረጃ መጠን ይገድቡ። ይህን ማድረግ፣ ግኙነት በተቋረጠበት ሁኔታ ዘገባ ላይ እያሉ በቁጥጥር ስር ቢውሉ፣ እርስዎንም ሆነ ምንጮችዎን በተሻለ መልኩ ለመከላከል ይረዳዎታል። 
  • ከሌሎች ጋር ለመገናኘት/ ለመነጋገር ዳር እስከ ዳር የተመሰጠሩ የመልእክት መላላኪያ መተግበሪያዎችን ይጠቀሙ፡፡ ዳር እስከ ዳር ምስጠራ ማለት ጥሪዎችን ጨምሮ በመተግበሪያዎ በኩል የተላከው ይዘት የተመሰጠረ ስለሆነ መልክቱ በሚጓጓዝበጥ ውስጥ ጣልቃ መግባት አይቻልም ማለት ነው፡፡ ለዚህ አይነቱ ግንኙነት ሲግናል እና ዋትስአፕ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መተግበሪያዎች ናቸው::  የእነዚህ መተግበሪያ ባለቤቶች የመልዕክቶችን ይዘት ማወቅ ስለማይችሉ፣ በመንግስትም የመረጃ ስጡኝ ጥያቄ አይኖርባቸውም፡፡ እነዚህ አገልግሎቶች እንዲያጡ ታግደው ከሆነና መጠቀም ሳይችሉ ቀርተው፣ በቴሌኮሙኒኬሽን ኩባንያ በኩል የሚያልፉ አጫጫጭር ምልዕቶች እና የስልክ ጥሪዎችዎ ቢያስትላልፉ  ሊጠለፉበዎ እንደሚችሉ ይወቁ ፡፡

ለግንኙነቶች መጥፋት/መቋረጥ መዘጋጀት

  • የበይነመረብ ወይም የግንኙነቶች መዘጋት መቼ ሊከሰት እንደሚችል ይተንብዩ። በይነመረብ ሊዘጋባቸው የሚችሉ ጊዚያት የሕዝባዊ አመጽን፣ የተቃውሞ ሰልፎችን እና የምርጫ ወቅቶችን ያካትታል፡፡ አንዳንድ የሀገሪቱ ክልሎች፣ ከሌሎቹ በበለጠ ለበይነመረብ ገደቦች የተጋለጡ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን ከዚህ በፊት የኢትዮጵያ መንግስት በሀገር አቀፍ ደረጃ ግንኙነትን የዘጋ ቢሆንም፣ በቅርብ ጊዜ የተደረጉ መቋረጦች የታዩት በትግራይ እና በምእራብ ኦሮሚያ እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
  • የበይነመረብ ግንኙነቶች ሙሉ በሙሉ ሊዘጉ በሚችሉበት ወቅት ስለሚኖረዎት እቅድ ከዜና ክፍልዎ እና ከሥራ ባልደረቦችዎ ጋር ይነጋገሩ። የት እና መቼ በአካል እንደምትገናኙ ዝርዝር እቅድ ይኑረዎ። በይነመረቡንም ሳይጠቀሙ እንዴት መረጃዎችን ለአዘጋጆች በሰነድ ማስተላልፍ የሚያስችለዎን ዘዴ ይፍጠሩ፡፡ የመደበኛ የመስመር ስልክዎን አድራሻ ማጋራትም ያስቡ፤ ነገር ግን፣ መደበኛ የስልክ ጥሪዎች ደህንነታቸው የተጠበቀ ስላልሆኑ ሚስጥራዊ ውይይቶችን መጠቀም እንደማያስችሎዎ ይገንዘቡ። የግኙነት መቋረጥ ሊገጥሟቸው በሚችሉ ክልሎች ወይም አካባቢዎች ውስጥ ሊኖሩ እና ሊሠሩ የሚችሉ የሥራ ባልደረቦቸዎን እንዴት መደገፍ እንዳለብዎም ያቅዱ።
  • ግንኙነት ከመቋረጡ በፊት ሊያስፈልጉኝ ይችላሉ የሚሏቸውን በኢንተርኔት ላይ የሚገኙ ማናቸውንም ሰነዶች ወይም ይዘቶች ያትሙ።
  • ግንኙነት በሚቋረጥበት ወቅት፣ መረጃዎችን ለማከማቸት ዩኤስቢ ድራይቮችን ወይም ሲዲዎችን በስረዎ ለሚስሩ ሰዎች ያቅርቡ። 

በይነመረብ መዘጋት ወቅት፣ በይነመረብን የማግኘት እድል ያላቸው እንድ ኤምባሲ ወይም ባንኮች ያሉ መስርያቤቶች ውስጥ የሚሰሩ ሰዎችን ወይም አገልግሎቶችን ለየትው ይወቁ፡፡ በይነመረብ ላይ ያለን መረጃ ሊያገኙልዎ ይችሉ እንደሆነ አስቀድመው ያነጋግሩዋቸው።

ትክክለኛዎቹን መሳሪያዎች መምረጥ

የመስመር ላይ መሳሪያዎች እና አገልግሎቶች ለደህንነት ጥሰቶች የተጋለጡ ናቸው። ጋዜጠኞች፣ በተለይ እንደ የመልዕክት መላላኪያ መተግበሪያዎች ያሉ የግንኙነት መሳሪያዎችን በተመለከተ፣ የቅርብ ጊዜውን የዲጂታል ደህንነት መረጃ እንዲተገብሩ ይመከራሉ፡፡ የሚከተለው ምክር ግንቦት 2013 ጀምሮ የሚያገለግል ነው፡፡

  • በይነመረብ በከፊል በሚዘጋበት ጊዜ፣ የታገዱ ጣቢያዎችን ለማግኘት እንዲረዱዎት የቪፔኤን አገልግሎቶችን ያውርዱ እና ያዋቅሩ፡፡ የበይነመረብ አገልግሎት አቅራቢዎች ቪፒኤንዎችን በተደጋጋሚ ያግዳሉ፤ ስለሆነም፣ በርካታ አማራጮች እንዲያዘጋጁ ይመከራል፡፡ ቪፒኤንን መጠቀም፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ሕገወጥ አይደለም፤  ይሁን እንጀ፣ የአከባቢው ባለሥልጣናት ሕጉን በተለየ መንገድ በመተርጎም ቪፒኤን መጠቀምን ሊከለክሉ እንደሚችሉ ጋዜጠኞች መገንዘብ አለባቸው።  በይነመረብ ሙሉ በሙሉ በሚመዘጋት ወቅትቪፒኤንን መጠቀም፣ ዋጋ የለውም።
  • ከሌሎች ጋር ለመገናኘት ከአንድ በላይ አማራጮች ይኑረዎት፡፡ የተለያዩ የግንኙነት መተግበሪያዎችን ማውረድ እና ማዋቀር አንዱ ከታገደ ወደሌላው በቀላሉ ለመዞር ያስችለዎታል፡፡ ከተለያዩ መተግበሪያዎች ጋር ሊኖሩ ስለሚችሉ የደህንነት ተጋላጭነቶች ይወቁ፡፡ ለምሳሌ፣ አንዳንድ አገልግሎቶች፣ በራሳችው በመብራት ፋንታ፣ ምስጠራን ራስዎ እንዲያበሩ ሊፈልጉ ይችላሉ። በበይነመረብ መዘጋት ወቅት እ ይበልጥ ደህንነታቸው ባልተጠበቀ መንገዶች እንደ አጫጭጭር መልዕክት መላላኪያ መልዕክት ለመለዋውጥ ሊገደዱ ይችላሉ፤ ስለሆነም፣ ሚስጥራዊ መረጃዎችን እንዴት እንደሚያጋሩ ልብ ይበሉ፡፡
  • ብሉቱዝ፣ ዋይፋይ ዳይሬክት እና ኒር ፊልድ ኮሙኒኬሽንን (Near Field Communication) በመጠቀም እንዴት መረጃዎችን ማጋራት እንደሚችሉ ይወቁ። እነዚህ ዘዴዎችን በመጠቀም፣ ያለበይነመረብ ስልክዎን ከሌላው ሰው ስልክ ጋር በማጣመር መረጃን ለማስተላለፍ ያስችሉዎታል። እነዚህ መሳሪያዎች በመደበኛነት በስልክዎ የቅንብር ክፍል ውስጥ ሊገኙ ይችላሉ። የበይነመረብ  መቋረጥ ከመከሰቱ በፊት አጠቃቀማቸውን ይለማመዱ። እንዲሁም ሚስጥራዊ ፋይሎችን በማጋራት ረገድ ያላቸውን ውሱንነት ይገንዘቡ፡፡
  • እንድ ብሪያር (Briar) ወይም ብሪጅፊይ(Bridgefy) ያሉ የአቻ-ለ-አቻ መልዕክት መላላኪያ መሣሪያዎችን ያውርዱ እና ያዘጋጁ፡፡ ብሪያር፣ በበይነመረብ፣ በዋይፋይ ቀጥታ እና በብሉቱዝ የሚሰራ ከዳር-እስከ-ዳር የተመሰጠረ የመልዕክት መተግበሪያ ነው። ብሪጅፊይ ከብሪየር ዝቅ ያሉ የደህንነት ማስጠብቂያ ባህሪያት ቢኖሩትም፣ በረጅም ርቀት ላይ የተሻለ ይሠራል።
  • ሮሚንግ ወይም የሳተላይት ስልክ ባለው ዓለም አቀፍ ሲም ካርድ በይነመረብን ሊያገኙ ይችላሉ፡፡ እነዚህ አማራጮች ውድ ከመሆናቸውም በላይ የሳተላይት ስልኮችን ወደ ኢትዮጵያ አስመጥቶ  ለመጠቀም፣ ጋዜጠኞች ከባለስልጣናት የቅድሚያ ፍቃድ ማግኘት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በተለይ፣ የአካባቢ ቅኝትን (location tracking) የሚዘግቡ ከሆነ እነዚህን አገልግሎቶች መጠቀምዎ ሊያስከትልብዎ የሚችለውን የደህንነት አደጋ ይወቁ፡፡ የውጭ ጋዜጠኞች፣ የእጅ ስልኮቻቸውን ኢትዮጵያ ውስጥ የሚጠቀሙ ከሆነ መሳሪያቸው በመንግስት ባለቤትነት ከሚገኘው ኢትዮ ቴሌኮም (ኢቲሲ) ጋር እንደሚገናኝ ማወቅ አለባቸው፤ ይህም ማለት፣ መንግስት የሚገኙበትን ስፍራ መከታተል ይችላል ማለት ነው፡፡

በግንኙነት መጥፋት ወቅት

  • በይነመረብ በተቋረጥብት ወቅት ሲዘግቡ፣ እንደ ሁኔታው፣ ለእስር ተጋላጭነትዎ ሊጨምር ይችላል። ስለሆነም፣ መሣሪያዎቸዎ፣ እርስዎንም ሆነ ሌሎችን ለአደጋ ሊያጋልጡ የሚችሉ ሚስጥራዊ መረጃ እንዳልያዙ ያረጋግጡ፡፡
  • ልክ በሰአቱ ሪፖርት ማድረግ አስቸጋሪ ቢሆንብዎትም እንኳ፣ ምን እየተከናወነ እንዳለ መሰነድ ይችላሉ፡፡ መረጃን ለማከማቸት እና ለሥራ ባልደረቦችዎ እና ለዜና አዘጋጆቸዎ ለማስረከብ ዩኤስቢዎችን ወይም ሲዲዎችን ይጠቀሙ። ከተቻለ፣ መርጃዎቸዎን ያመስጥሩ፡፡ በእነዚህ መሳሪያዎች ላይ መረጃ ባልተመሰጠረበት ሁኔታ በቁጥጥር ስር ከዋሉ፣ መርጃዎችን ባለስልጣናቱ ሊያገኟቸው እንደሚችሉ ይወቁ፡፡
  • ብሉቱዝን፣ ዋይፋይ ዳይሬክትን ወይም ኤን.ሲ.ሲን በመጠቀም በመሣሪያዎች መካከል ፋይሎችን ያጋሩ (እነዚሀ ነገሮች ብዙውን ጊዜ በመሣሪያው ቅንብሮች ስር ይገኛሉ)። በዚህ መንገድ መረጃን ማስተላለፍ ደህንነቱ የተጠበቀ አለመሆኑንም ይገንዘቡ፤  መሣሪያዎ በአቅራቢያ ካሉ የማይታወቁ መሣሪያዎች ጋር እንዳይገናኝ ለማስቻል የሚጠቀሙበትን ማንኛውም ነገር ተጠቅመው ሲጨርሱ ይዝጉት።
  • እንደ ብሪር እና ብሪድፊ ያሉ የአቻ-ለ-አቻ የግንኙነት መተግበሪያዎችን ይጠቀሙ፡፡ ይሁንና እነሱን መጠቀም ሊያስከትላቸው ከሚችሉ የደህንነት አደጋዎችም ይጠንቀቁ፡፡
  • ግንኙነት በሚዘጋበት ጊዜ፣ ሚስጥራዊ መረጃ ለማግኘት እንደ አጫጫር መልዕክት መላኪያ ወይም የስልክ ጥሪዎች ያሉ ደህንነታቸው ያልተጠበቀ የግንኙነት ዘዴዎችን ከመጠቀም ለመቆጠብ ይሞክሩ፡፡ እነዚህ የግንኙነት ዘዴዎች በመንግስት ባለቤትነት በሚተዳደረው የቴሌኮሙኒኬሽን አቅራቢ በኩል፣ በኢትዮጵያ መንግስት ሊጠለፉ ወይም ሊደርስባቸው ይችላሉ፡፡
  • የአንድሮይድ ስልክ ተጠቃሚዎች፣ ከበይነመረቡ ጋር ግንኙነት ሳያስፈልጋቸው መተግበሪያዎችን ለማውረድ ኤፍ-ድሮይድን (F-Droid) መጠቀም ይችላሉ፡፡ ለአንድሮይድ ሌላ አማራጭ መተግበሪያን ለመጫን የኤ.ፒ.ኬ ፋይልን መጠቀም ይበጃል፡፡ እነዚህ የመተግበሪያ ፋይሎች ከመተግበሪያ መደብር (store)ጋር ሳይገናኙ በመሣሪያዎች መካከል ሊጋሩ ይችላሉ፤ ይሁን አንጅ፣ የመተግበሪያ መደብር ማጣሪያ አይደረግባቸውም፤ ስለሆነም እንሱን ሲጠቀሙ ከሚያምኗቸው ሰዎች ብቻ ፋይሎችን ይቀበሉ።
  • የታገዱ ገጾችን በስክሪን ሾት በማንሳት፣ ስለመዘጋታቸው ይሰንዱ፡፡ ይህንን ሰነድ፣ በአገርዎ ወይም በዓለም አቀፍ-ደረጃ ለሚንቀሳቀሱ የዲጂታል መብት ተሟጋች ድርጅቶች በሌላ ጊዜ ሊያጋሯቸው ይችላሉ፡፡  ይህን ማድረግ ግን ለአደጋ ሊያጋልጥዎ እንደሚችል ልብ ይበሉ ፡፡

ከግንኙነቶች መጥፋት በኋላ

  • ስለ በየነመረብ መዘጋት ዝግጅት እየተደረገ ባለበት ሁኔታ፣ የትኛው ዘዴ እንደሠራ እና  የትኛው እንዳልሠራ ከዜና ክፍልዎ ወይም ከሥራ ባልደረቦችዎ ጋር ይነጋገሩ፡፡
  • መሣሪያዎችዎን ይፈትሹ፤ ምትክ በማስቀመጥ ይዘተዎን ወደ ውጫዊ ማከማቻ ወይም ወደ ክላወድ ያስተላልፉ። በሚቻልበት ጊዜ ሁሉ፣ ደህንነቱ ይበልጥ የተጠበቀ እንዲሆን ለማድረግ መረጃዎን ያመስጥሩ።

የዲጅታል ደህንነት፤ እራስን ከማስገር (Phishing) ስለመከላክል

የማስገር ዘመቻዎች፣ በምርጫ ወቅት ሊጨምሩ ይችላሉ።  ኢትዮጵያውያን ተቃዋሚዎች፣ ጋዜጠኞች እና የሚዲያ ተቋማት ከዚህ ቀደም የተራቀቁ የአስጋሪ የጥቃት ሰለባዎች ሆነው ቆይተዋል።  ሲቲዝን ላብራቶሪ እና ግላዊነት ኢንተርናሽናል (Citizen Lab and Privacy International) እንደዘገበው፣ የዚህ አይነቱ ጥቃት፣ በየመሣሪያዎች ላይ እየተጫኑ ላሉ የንግድ ስፓይዌሮች ምክንያት ሆኗል። ሰለ ምርጫ፡ ዘመቻው የሚዘግቡ ጋዜጠኞች በኢሜል እና በመልዕክቶች የተላኩ ሰነዶች እና ሊንኮች ሲያጋጥሟቸው የተለየ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል ። በዚህ ረገድ፣ ምርጥ ተሞክሮዎችን የያዙ ምክሮች ከዚህ በታች ተዘርዝረዋል።

አጠቃላይ ምርጥ ተሞክሮዎች

  • በመልዕክቶች ወይንም በኢሜል አማካኝነት የተላከለዎትን ሊንክ ተጠቅመው ፋይሎችን ከማወረድ ይልቅ፣ ሁሌም ግልጋሎቱን በሚሰጡ ድር-ገጾች የሚገኙ ሶፍትዌሮችን ያውርዱ። 
  • በጥድፊያ አንድ ነገር እንዲያደርጉ ከሚገፋፉዎ ውይንም ደግሞ ለማመን የሚያዳግቱ የሚያማልሉ ነገር የሚሰጥዎ መስለው ከሚታዩ መልዕክቶች ይጠንቀቁ ፣ በተለይም አገናኙን ጠቅ ማድረግ ወይም ዓባሪን ማውረድ የሚያካትቱ ከሆነ።
  • የመልዕክቱን እውነትኛነት ለማወቅ፣የላኪውን አካውንትና የመልዕክቱን ዝርዝር ሁኔታ በደንብ ይፈትሹ።  በፊደል አጻጻፍ፣ በሰዋስው፣ በመልዕክቱ አቀማመጥ፣ ወይም ቃና የሚታዩ ትናንሽ ልዩነቶች አካውንቱ እንደተጭበረበረ ወይም እንደተጠለፈ ሊያመለክቱ ይችላሉ።
  • በሞባይል ስልክ ኩባንያዎ ወይም በተንቀሳቃሽ ስልክዎ በኩል የሚመጣ ማንኛውም አጫጫር መልዕክት ወይም የስልክ ጥሪ ደህንነቱ ያልተጠበቀ እና ክትትል የሚደረግበት ሊሆን እንደሚችል ያረጋግጡ።
  • የደረሰዎት መልዕክት ከሚያውቁት ሰው የመጣ ቢመስልዎም እንኳን ሊንኮችን ከመጫነዎ በፊት በጥንቃቄ ያስቡ። የዩ.አር.ኤሉን(URL) ትክክለኛነት ለማረጋጥ ከርሰርዎን በሊንኩ ላይ እንዲያንዣብብ ያድርጉ።
  • በኢሜል የሚቀበሉትን ማናቸውንም አባሪ አስቀድመው ይመልከቱ። ሰነዱን ካላወረዱ ማንኛውም ተንኮል አዘል-ዌር ባለበት ተይዞ እንዲቆይ ማድረግ ይቻላል፡፡ ጥርጣሬ ካለዎት ለላኪው ይደውሉና ይዘቱን በኢሜል ውስጥ ገልብጠው እንዲልኩለዎት ይጠይቋቸው፡፡
  • በወሬ ቡድኖች አማካኝነት በሚላኩ ሊንኮችና ሰነዶች ላይ ይጠንቀቁ። በርካታ ቁጥር ያላቸው የወሬ ቡድኖች ዘንድ፣ ባልስጣናት ወይንም ተሳታፊዎችን ለማጥመድ የፈለጉ ሌሎች ሰዎች ሰርገው ሊገቡ ይችላሉ
  • መልዕክቶችን ለመገምገም/ለመፈተሽ የዴስክቶፕን መተገብሪያዎች ይጠቀሙ።  ትልቅ ስክሪኖችን መጠቀም የተቀበሉትን መልዕክት ምንነት ለማዎቅ ይረዳውታል፤ እናም ብዙ ተግባራትን የመጠቀም እድለዎም ያነሰ ይሆናል። 
  • አጠራጣሪ ሊንኮች እና ሰነዶችን ቫይረስ ቶታል ላይ ይስቀሉ። ቫይረስ ቶታል ተንኮል አዘል ዌርን ለመለየት የሚያስችል አግልግሎት ነው፤ ይሁን እንጂ፣ ብዙ ጊዜ የሚታወቁትን ብቻ ለመቃኘት እንደሚያስችል መገንዘብም ተገቢ ነው።
  • ራስ-ሰር ማዘመኛዎችን እንዲሰሩ በማድረግ በየመሣሪያዎችዎ ላይ ያሉ ሶፍትዌሮችን ሁሉ ወቅታዊ ያድርጉ። ይህንን በማድረግ፣ ደህንነትዎን የሚያደናቅፉ ተንኮል አዘል ዌሮችን የሚያስከትሉ የታወቁ ተጋላጭነቶችን ማስተካክል ይቻላል።
  • ምርጫ በሚከናወንበት ጊዜ እና በሁከትና በብጥብጥ ወቅት ወይም ባልደረቦቸዎና በአካባቢው ያሉ የሲቪል ማህበራት ጥቃት እንደደረሰባቸው ሪፖርት ማድርጋቸውን ተክትሎ ሊከሰቱ የሚችሉ የፊሺንግ ሙከራዎችን በንቃት ይከታተሉ።

የዲጂታል ጥንቃቄ፤ የመስመር ላይ ጥቃት እና የተሳሳተ መረጃ ዘመጃዎች 

በመርጫ ወቅት፣ በተለይ አዘጋገቡ መንግስትን በጣም በሚያጥላላ ወይም በጣም በሚደግፍ ሁኔታ ተቃኝቶ በሚሰራብት ጊዜ፣ በሲፒጄ እንደተሰነደው፣ በእነሱ ላይ ያነጣጠረ ጥቃትን ጨምሮ፣ ጋዜጠኞች የመስመር ላይ የትንኮሳ ሰለባ የመሆናቸው አጋጣሚ ከፍተኛ ነው። በመስመር ላይ፣ የገዢው ፓርቲ ደጋፊዎችም ሆን ተቃዋሚዎች ንቁ ተሳታፊዎች ናቸው።  ትግራይ ውስጥ ሆነው የሚዘግቡ ጋዜጠኞች የመስመር ላይ ጥቃት እና ሀሰታኛ መረጃን ታሰራጫላችሁ የሚል ክስ ሊግጥማቸው እንደሚቸል ልብ ሊሉ ይገባል። የዲጅታል መብት ኔትዎርክ ለአፍሪካ የተሰኘው ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት እንደዘገበው፣ ጥቃቶች፣ የተቀነባበሩ የትዊተር ዘመጃዎችን አቋቁመው በሚያጧጡፉ የመንግስት ተቃዋሚ የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ማሕበርስቦች ሊፈጸሙ ይችላሉ። ጋዜጠኞች እራሳቸውንና አካውንቶቻቸውን ከጥቃት በተሻለ ለመከላከል የሚያስቸሏቸው የተለያዩ ዘዴዎች አሉ። 

የጥቃትን ስጋት ለመቀነስ

  • የጠቅላላ የምርጥ ተሞክሮ በሚለው ክፍል እንደተገልጸው፣ 15 ፊደላትን ወይም ከዚያ በላይ የያዙ የይለፍ ቃላትን እና የይለፍ ቃል ማኔጀርን በመጠቀም፣ አካውንቶዎቸዎን በ2ኤፍኤ ደህንነታቸውን ይጠብቁ። የይለፍ ቃላትን በድጋሚ አይጠቀሙ። 
  • የተለያዩ የመፈለጊያ ኢንጆኖችን (search engines) በመጠቀም ስመዎን ይፈልጉና ከህዝብ እይታ መውጣት አላባቸው የሚሏቸውን እርሰዎን የሚመለከቱ መርጃዋች ያጥፉ። 
  • የማህበራዊ ሚዲያ አካውንቶቸዎን በሚገባ ያጢኑና ማንነቴን ሊያሳውቁብኝ የሚሏቸውን የግል መረጃዎች ያስወግዱ ወይንም ይቀንሱ። ከህዝብ እይታ ውጭ መሆን አለባቸው የሚሏቸውን እንድ ስልክ ቁጥረዎ ያሉ የግንኙነት መረጃዎቸዎን ያስወግዱ። 
  • አካውንቶቸዎን በውል በማጤን፣ እኔን ለማጥላላት ሊያገለግሉ የሚሏቸውን ፎቶዎች ወይንም ምስሎች ያሰወግዱ። 
  • የዲጂታል ማስፈራሪያዎች ውደ አካለዊ ጥቃቶች ሊያመሩ ስለሚችሉ እንደዚህ አይነቶችን ምልክቶች ለማየት ይችሉ ዘንድ አካንቶቸዎን ባንክሮ ይከታተሉ።  የትኞቹ ምልክቶች የበለጠ ስጋትን ሊያስከትሉ ይችላሉ የሚለውን በተመለከተ ከዚህ በታች የቀረበውን ዝርዝር ይመልከቱ። 
  • ስለመስመር ላይ ትንኮሳዎች ለቤተስቦቸውና ለጓደኞዎቸዎ ያዋዩ። የመስመር ላይ አጥቂዋች ብዙ ጊዜ ስለጋዜጠኞች የሚፈልጉትን መረጃ የሚያገኙት በዘመዶቻቻው ወይንም በዙርያቸው ባሉ ሰዎች የሚዲያ አካውንቶች አማካኝነት ነው። ቤተስቦቸዎንና ጓደኞቸዎን ፎቶቸዎን እንዲያስዎግዱለዎት ዎይም የእይታቸውን መጠን እንዲቀንሱለዎት ይጠይቋቸው። 
  • ከቻሉ፣ በመስመር ላይ በተቃጣ ጥቃት የተነሳ ቤተዎን ለቀው የመውጣት እቅድ ካለዎት፣ ለዋና አዘጋጁ ይንገሯቸው። በግለዎ የሚሰሩ ጋዜጠኛ ክሆኑ ደግሞ፣ ስለመስመር ላይ ጥቃቱና ባስፈላጊ ጊዜ ሊጠቀሙባቸው ስለሚችሉ የድጋፍ አገልግሎቶች ስለማቋቋም ለስራ ባልደረቦቸዎ ያሳስቧቸው

በጥቃት ጊዜ

  • ከጥቃቱ በስተጀርባ ያሉ ማን እንደሆኑና አላማቸው ምን እንደሆነ ለማጣራት ይሞክሩ። ይህን ማድረግ የአካላዊውን የማስፈራሪያ ስጋት ልክ ለማወቅ ይረዳወታል። 
  • መልዕክቶችን በደንብ በመመልከት፣ ለአካላዊ ጥቃት የመዳረገዎ የስጋት ደረጃ ምን ያህል እንደሆነ ያጢኑ።  በመስመር ላይ እየተንሸራሸሩ ያሉ መልዕክቶች የቤተዎን አድራሻ ወይንም የስልክ ቁጥርዎን የያዙ ከሆነ፣ የአደጋው የስጋት መጠን ከፍ ያለ ነው ማለት ያስችላል። መልዕክቶቸን ማየት የማልችልበት ሁኔታ ነው ያለሁ ብለው ካስቡ፣ የሚያምኗቸው ጓደኛዎ ወይንም የስራ ባልደራበዎ እንዲያዩለዎ ይጠይቍ።
  • የዛቻ መልዕክቶችን ፣ መልዕክቶቹ የተላለፈበትን ቀንና ሰዓት እና የተላለፈባቸውን የማህበራዊ ሚዲያዎችን አካተው የያዙ ስክሪንሾቶችን ጨምሮ፣ አሳሳቢ የሆኑ መልዕክቶችን እና ምስሎችን ሰንደው ይያዙ።  የኋላ ኋላ ስለ ጥቃቱ ለማህበራዊ ሚዲያ ድርጅቶች፣ ለዜና አዘጋጅዎ፣ ሀሳብን በነፃነት ስለመግለጽ ለሚሟገቱ ድርጅቶች እና ስለጥቃቱ ለባለስልጣናት ሪፖርት ማድረግ ቢያስፈለግዎት፣ የዚህ አይነቱ መረጃ ሊጠቅመዎት ይችላል። 
  • የመስመር ላይ ትንኮሳ እየደረሰበዎ እንደሆነ ለቤተሰበዎ፣ ለተቀጣሪዎቸው፣ እና ለጓደኞቸው ይንገሯቸው።
  • ብዙውን ጊዜ ባላጋራዎቸው የቤተሰበዎን አባላት እና ጓደኞቸዎን ያገኟቸዋል፤ ያ ደግሞ የማዋክቡ ኡደት አንድ አካል ነው። 
  • የሚላኩለዎትን መልዕክቶች በማገድ፣ መልስ ባለመስጠት እና ለመልዕክቶቸዎ መልስ ሊሰጡ የሚችሉትን ሰዎች ቁጥር በመገደብ ችግሩን ለመቅረፍ የሚረዱ እርምጃዎች ናቸው፤ ይሁን እንጅ፣ እነዚህን እርምጃዎች መውስዱ፣ ከሰዎች ጋር የሚያደርጉትን የመስመር ላይ ግኑኝነት ከመገደቡም በላይ፣ የማስፈራሪያ መልዕክቶች እንዲያመልጡዎ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ።  
  • ትንኮሳው እስኪያከትም ድረስ፣ አብዛኛወቹን የማህበራዊ ሚዲያ አካዎንቶቸዎን የግል ለማድረግ ያስቡ። 
  • ከዜና ክፍለዎ ጋር በመሆን ለመስመር ላይ ትንኮሳዎች መቸ እና እንዴት ምላሽ መስጠት እንዳለበዎ ይወስኑ። ለእያንዳንዱ መልዕክት ምላሽ መስጠት አዋጭም ጠቃሚም አይደለም።  ይሁን እንጅ፣ የተሳሳተ የመረጃ ዘመቻ ወቅት ከእርስዎ የዜና ክፍል የሚገኘውን የድጋፍ መልዕክት በእርስዎ እና በማኅበራዊ ሚዲያ አናት ላይ እንዲቀመጥ ማድረግ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል
  • የመስመር ላይ ትንኮሳ ከፍተኛ የሆነ የመገለል ስሜት ሊፈጥር ይችላል፡፡ እርስዎን ለማገዝ የሚረዱ የድጋፍ ትስስሮች እንዲኖረዎ ያድርጉ። ይህን ማድረግ፣ ነገሮች በጎ በሆኑ ጊዚ፣ አሠሪዎንም ያካትታል። በመስመር ላይ ጥቃት በሚከሰትበት ጊዜ የአእምሮ ጤንነትዎን ለመጠበቅ የሚረዱ የበለጡ መረጃዎች ለማግኘት የሲ.ፒ.ጄን የደህንነት ማስታወሻ ይመልከቱ።

ማጠቃለያ፡ የአዘጋጆች የደህንነት ማረጋገጫ ዝርዝር

የዜና አዘጋጆች፣ የሚዲያ ሰራተኞችን በአጭር ጊዜ ማሳሳቢያ ከምርጫ ጋር የተያያዙ ኩነቶችን እንዲዘግቡ ሊጠይቋቸው ይችላሉ፤ አዘጋጆቹ ይህንን በሚያደርጉበት ጊዜ፣ የሚዘገበው ሁነት በድንገት ወደ ግጭት ሊያመራ እንደሚችል፣ ሁነቱ የሚዘገበው በጣም ከራቀ አካባቢ ሊሆን እንደሚችል ወይም ደግሞ አካባቢው በብሔር መቆራቆሰና ግጭት የሚታምስ ሊሆን እንደሚችል ግምት ውስጥ ማስገባት አለባቸው።  ይህ የደህንነት ማረጋገጫ ዝርዝር በሠራተኞች ላይ ሊደርሱ የሚችሉ አደጋዎችን በመቀነስ ረገድ ሊነሱ የሚችሉ ዋና ዋና ጥያቄዎችን እና መወሰድ የሚገባቸውን እርምጃዎች አካትቷል።

ጠቃሚ ማስታወሻ፤ የሚከተሉት ጠቃሚ ነጥቦች እንደ መፍትሄ ፈላጊዎች፣ ቦታ አመላካቾች እና የትርጉም ስራ በሚስሩ የአካባቢው ወገኖች ዘንድ ሊታወቁ ይገባል::

ስሰራተኞች ሊታሰቡ/ግምት ውስጥ ሊገቡ የሚገባቸው ጉዳዮች 

  • የተመረጡት ሰራተኞች የሚመደቡበትን የሚመጥን በቂ ልምድ አላቸው ወይ? 
  • ከተመረጡት ሰራትኞች መካከል ለኮቪድ ስጋት ከተጋለጡ ወገኖች ውስጥ የሚፈረጁ ወይም የእነርሱ እርዳታ የግድ የሚያስፈልጓቸው የቤተሰብ አባላት/የእነሱ ጥገኞች ያሏቸው አሉ ወይ ? ከሆነስ፣ የሚፈለገውን የክትባት መጠን ወስደዋል ወይ?  
  • ከተመረጡት ሰራተኞች መካከል፣ የማንነት መገለጫዎቻቸው፣ ብሄራቸው ወይም ማንነታቸው የጥቃት ኢላማ ሊያደርጋቸው የሚችሉ ሰዎች አሉ ወይ? የሚዲያው መስሪያ ቤት ፖለቲካዊ ወገናዊ ትስስር በጋዜጠኞቹ ላይ ለያስከትል የሚችለው አደጋ አለ ወይ? 
  • የተመረጡት ሰራተኞች ስራቸውን ለመስራት የሚያስችል የተሟል አካላዊ ብቃት አላቸው ወይስ በስራቸው ላይ ተፅእኖ የሚያሳድር የጤና እክል አለባቸው? 
  • ከተመረጡት ሰራተኞች መካከክል የተለየ የስራ ድርሻቸው የበለጠ አደጋ ላይ ሊጥላቸው የሚችሉ ሰራተኞች (ለምሳሌ፣ በፎቶ ጋዜጠኝነት ተመድበው እድርጊቶች መሃል የሚሰሩ) አሉ ወይ? 

መሳሪያና ትራንስፖርት

  • ከቡድንዎ አባላት እንዴት ግንኙነት እንደሚፍጥሩና አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም እንዴት እራሳቸውን ከሁኔታው ሊያገሉ እንደሚችሉ፣ ሁኔታዎችን አመቻችተዋል ወይ?  መሬት ላይ ያሉ የግንኙነት መስመሮች ሙሉ በሙሉ መቋረጥ፣ ሁኔታዎችን እንዴት ሊያወሳስብ እንሚችል ልብ ይብሉ። 
  • የእጅ ስልካቸውን ጨምሮ፣ ስራተኞች ለመሳሪያዎቻቸው ምትክ በማዘጋጀት ተገቢውን ጥንቃቄ አድርገዋል ወይ? 
  • ለግንኙነት መንገዶች ተገቢውን ጥንቃቄ ስለማድረጋቸውና አግባብነት የመላላኪያ መተገብረያዎችን ስለማውረዳቸው ሰራተኞችን አነጋገረዋቸዋል ወይ?
  • ሰራተኞች ስለሚሄዱብት መንገድ ደህነነት፣ በዛ መንገድ በቅርቡ ስለተክሰቱ ሁነቶች ወይም ነውጦች እና ሊኖሩ ሰስለሚችሉ የፍተሻ ኬላዋች በቂ ጥናት አድርገዋል ወይ? 
  • ግጭት ሊከሰት ይችላል ተብሎ በሚገመትበት ሁኔታ፣ እንደ ሄልሜት ያሉ እራስን ለመከላከል የሚያስችሉ ቁሳቁሶችን አዘጋጅተዋል ወይ? በስረዎ ያሉ ሰራትኞችስ ስለ እነዚህ እራስን ለመከላክል ስለሚያገልግሉ መሳሪያዎች አጠቃቀም ያውቃሉ ወይ? 
  • አንዳንድ የተመረጡ ሰራትኞች እራሳቸው ናቸው መኪናዎችኝን የሚያሽከረክሩት? መኪናዎችስ ምን ያህል አስተማማኝ፣ ተገቢ እና ወጣ ገባውን የመንገድ ሁኔታ ለመቋቋም የሚያስችል ጥንካሬ አላቸው? 
  •  ስለ ኮቪድ አደገኛነት ተጋላጭነት ከተመረጡ ሰራትኞች ጋር ተወያይታችኋል ወይ? ጥራቱን የጠበቀ ያአፍና የአፍንጫ ጭንብል እና የአልኮል ሳኒታይዝሮችንስ አቅረበውላቸዋል ወይ? 

ትኩረት ሊሰጥባቸው የሚገባቸው አጠቃላይ ጉዳዮች 

  • ዘገባው ቢሰራ ሊገኝ ከሚችለው ጥቅም አንጻር፣ በተመረጡት ሰራትኞች ላይ ሊደርስ የሚችለው የጉዳት መጠን ተቀባይነት አለው ወይ? 
  • የተመረጡት ሰራተኞች ለድርጅተዎ እንደሚሰሩ የሚያመለክቱ ተገቢ የሆነ የሙያ ብቃት ማረጋገጫዎች፣ የይለፍ ወረቀቶች ወይም ደብዳቤ ተሰጥቷቸዋል ወይ? 
  • ለሰራ ስለተሰማሩ ሰራተኞቸዎ ያደጋ ጊዜ ተጠሪዎች ዝርዝር መረጃዎች መዝግበው በጥንቃቄ አስቀምጠዋል ወይ? 
  • (አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ) ስለመግቢያ/ስለመሳፈርያ የሚያሳዩ ዝርዝሮችን አዘጋጅታውል ወይ? 
  • የቡድኑ አባላት ተገቢ የሆነ ዋስትና እና የህክምና ሽፋን ተግብቶላቸዋል/ተመቻችቶላቸዋል?
  • በጉዳት ጊዜ የህክምና አገልግሎት የሚሰጡ የህክምና ተቋማት ለይተው አውቀዋል ወይ? ስለነዚህ ተቋማት የቡድነዎ አባላት እንዲያውቁ አድርገዋል ወይ? (አም. ኤስ. ኤፍ እንደገለጸው፣ ትግራይ ውሰጥ፣ ከሚገኙት የህክምና ተቋማት መሀል፣ 70% ገደማ የሚሆኑት ተዘርፈዋል ተብሎ እንደሚነገር ያስታውሱ)።  
  • ከስራው ጋር በተያያዝ ሊፈጠሩ ስለሚችሉ አስጨናቂ ሁነቶች አንስተው (ከቡድን አባላቶቸዎ ጋር) ተወያይተዋል ወይ? 

ስለ ስጋት ዳሰሳ እና እቅድ የበለጠ መረጃ ለማግኘት፣ የሲፒጄን የመረጃ/ የግብዓት ማዕከል ይመልከቱ